"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Saturday 12 October 2013

“አውጣኝ ያለም ወጣ አብላኝ ያለም በላ፣ምስኪኑ ጥንቸል ግን ተኝቶ ተበላ”

 
(ቴዲ - ዘአትላንታ)
ዕውቀት ጥራዝ ነጠቅ ከሆነ አስቸጋሪ ነው። ከጥራዝ ነጠቅ ሰው ጋር መከራከርም አይቻልም፣ ለሱ እሱ ልክ ነው፣ ምክንያት አምጥቶ፣ ብልት አውጥቶ አይከራከርም - የሚያውቀው ትችት ብቻ ነው። ጥራዝ ነጠቅነት ከስሜታዊነት ጋርም ይያያዛል። እንዲህ አይነት ሰዎች ፌስ ቡክ ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም ቦታ አሉ - ይኖራሉም።

ሰሞኑን ከዚሁ ዓይነት ጥራዝ ነጠቅነት የመጣው ሃሳብ “ለኢትዮጵያ ለምን ይጸለያል - ናይጄሪያም እኮ አምላክ አለው” የሚል ነው። እንዲህ ዓይነት አስተሳስብ ጥራዝ ነጠቅነት ይባላል - አንዲት ነገር ፣ በአንዲት ጎን እና በአንድ መነጽር ብቻ አይቶ የሚሰጥ ጭፍን ድምዳሜ ነው።
...
ስለኢትዮጵያ ማሸነፍ መጸለይ ፣ ከናይጄሪያ መጸለይ አለመጸለይ ጋር ምን ያገናኘዋል? አንድ ሰው ሎተሪ ቆርጦ አንደኛው ዕጣ እንዲደርሰኝ እርዳኝ ብሎ ቢጸልይ ፣ አይይ .. ብዙ ሰው ቆርጧልና ለሌላው አይድረስ ለኔ ብቻ ይድረስ ማለት ስለሆነ አትጸልይ ሊባል ነው? አንድ ሥራ ቦታ የተወዳደረ ሰው "እግዜር ይህን ሥራ እንዳገኝ ርዳኝ" ብሎ ቢጸልይ .. አይይ ብዙ ሰው ተወዳድሯልና ለኔ ብቻ ብለህ አትጸልይ! .. ሊባል ነው? ሁሉም የሚጸልየው እኮ ለራሱ ነው።

እኛ እንደኢትዮጵያዊ፣ ለኢትዮጵያ እንጸልያለን፣ ናይጄሪያኖችም ለራሳቸው ይጸልዩ .. እግዜር ደግሞ የፈቀደውን ይስማ። አንድ ታሪክ ጣል ላድርግ … አንድ አንበሳ ተራበና .. እባክህ አብላኝ አብላኝ እያለ ወደ ፈጣሪው ጸለየ ….. ጸሎቱን እንደጨረሰ ቀና ሲል አንዲት ሚዳቆ አየ። “አይ ፈጣሪ! ጸሎት እንዲህ ፈጥነህ የምትሰማ ተመስገን .. አለና ሊያዛት ሲሮጥ .. እሷም በበኩሏ ወደ ፈጣሪዋ “አውጣኝ፣ አውጣኝ፣ አድነኝ” እያለች በመጸለይ መሮጥ ጀመረች። እግዜር ማንን ይስማ? (ናይጄሪያም ይጸልያል፣ ኢትዮጵያም ትጸልያለች .. እግዜር ማንን ይስማ? ስለዚህ አንጸልይ ለሚሉት ነው ..) .. ታሪኩ ይቀጥላል .
…. አንበሳው ሲከተል፣ ሚዳቆም ስትሮጥ ቆዩ። መጨረሻ ላይ ሚዳቆ አመለጠች፣ አንበሳም ደክሞት እንደተራበ አረፍ ለማለት ሲሞክር ሳይጸልይ ተኝቶ የሚያንኮራፋ ጥንቸል አገኘ። “ተመስገን - ሚዳቆ ብትነሳኝ ጥንቸል ሰጠኸኝ” በማለት ምሳ አደረገው።
ያን ጊዜ እንዲህ ተባለና ተገጠመ
“አውጣኝ ያለም ወጣ አብላኝ ያለም በላ፣
ምስኪኑ ጥንቸል ግን ተኝቶ ተበላ”

እናም ጸሎት ምን ይሰራል፣ ተኙ የሚሉ ጥራዝ ነጠቆች “የ7 ቢሊዮን ሰው ጸሎት በአንድ ሰከንድ መስማት የሚችልን እግዜር ፣ ግራ አታጋቡት ሊሉ ይሞክራሉ። የሱን ጥበብ ማን ያውቃል? ናይጄሪያና ኢትይጵያ ቢሸናነፉ እንኳን ሌሎች አገሮች በተለያየ ምክንያት “ዲስኳሊፋይ” ተደርገው ሁለቱም ሊያልፉ ይችላሉ እኮ! .. የኛ ድርሻ መጸለይ ነው፣ ጸሎታችንን መስማት አለመስማት የእግዜር ነው። ከጥራዝ ነጠቅ ዕውቀት ይሰውረን!!