"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Sunday 17 February 2013

ወንድ ብቻውን ነው እሚያለቅስ

ወንድ ብቻውን ነው እሚያለቅስ
ጸጋዬ ገብረ መድኅን

ከወዳጅ ከዘመድ ርቆ
አንጀቱን በአንጀቱ ታጥቆ
ተሸሽጎ ተገልሎ፥ ተሸማቆ ተሸምቆ
ከቤተ-ሰው ተደብቆ
መሽቶ፥ የማታ ማታ ነው፥ ሌት ነው የወንድ ልጅ እንባው
ብቻውን ነው የሚፈታው፡፡ . . .
ብቻውን ነው የሚረታው፡፡ . . .
... ችሎ፥ ውጦ፥ ተጨብጦ፥ ተማምጦ ተጣጥሮ
በሲቃ ግት ተወጥሮ
እንደደመና ተቋጥሮ
እውስጥ አንጀቱ ተቀብሮ . . .
መሽቶ፥ ረፍዶ፥ ጀምበር ጠልቆ
የጨለማ ድባብ ወድቆ
በእንቅልፍ ጥላ ሲከበብ፥ በዝምታ ሲዋጥ አገር
ፍጡር ሁሉ ተስለምልሞ፥ ብቸኝነት ብቻ ሲቀር . . .

የኋላ የኋላ፥ ማታ
ምድር አገሩ በእፎይታ
ዓይኑን በእንቅልፍ ሲያስፈታ
ሁሉ በእረፍት ዓለም ርቆ፥ ብቸኝነት ብቻ ሲቀርብ
ያኔ ነው ወንድ ዓይኑ የሚረጥብ
የብቻ፥ እንባ ወዙ እሚነጥብ፡፡
ብቻውን ነው፥ ብቻውን ነው . . .
የእንባ ጭለማ ለብሶ ነው
ወንድ ልጅ ወዙ እሚነጥበው፡፡
ዕጣውን ለብቻው ቆርሶ
ብቻውን ሰቀቀን ጐርሶ
ብቻውን ጭለማ ለብሶ
ገበናውን ሣግ ሸፍኖ
ክብሩን በሰቆቃ አፍኖ
ሌሊት፥ የማታ ማታ ነው
ሕቅ እንቁን እሚነጥበው
ኤሎሄውን እሚረግፈው . . .
ከዓይኑ ብሌን ጣር ተመጦ
ከአንጀቱ ሲቃ ተቆርጦ
ደም አልሞ ፍም አምጦ
ከአፅመ-ወዙ እቶን ተፈልጦ
ከአንጀቱ ሲቃ ቆርጦ
ደም አልሞ ፍም አምጦ
ከአፅሙ ወዙ እቶን ተፈልጦ
እንደጠፍር-ብራቅ እምብርት
እንደእሳተ ገሞራ ግት
‘ርቅ ነው ወንድ ልጅ እንባው
ደም ነው፥ ፍም ነው እሚያነባው፤
ንጥረ ሕዋስ ነው ሰቆቃው
ረቂቅ ነው ምሥጢር ነው ጣሩ፥__ብቻውን ነው የሚፈታው፥
ብቻውን ነው የሚረታው፡፡
ችሎ፥ ውጦ፥ ተጨብጦ፥ ሰቀቀኑን በሆዱ አጥሮ
በአንጀቱ ገበና ቀብሮ
ውሎ ጭጭ እፍን ብሎ፥ እንደደመና ተቋጥሮ
ጣሩን ውጦ ተጣጥሮ
በሲቃ ግት ተሰትሮ፥ . . .
ከወዳጅ ከዘመድ ርቆ
ከቤተ-ሰው ተደብቆ
አንጀቱን በአንጀቱ ታጥቆ፥
ተሸሽጎ ተከናንቦ፥ ተሸማቆ ተሸምቆ . . .
የብቻ ብቸኝነቱ፥ የጭለማ ልብሱ እስኪደርስ
በዓይን አዋጅ ሃሞቱ እንዳይረክስ
ቅስሙ በገበያ እንዳይፈስ
ተገልሎ በእኩለ-ሌት፥ ወንድ ብቻውን ነው እሚያለቅስ፡፡
ጸጋዬ ገብረ መድኅን
እሳት ወይ አበባ
(፲፱፻፶፭ - አምቦ - ኮልፌ)

No comments:

Post a Comment