"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Thursday 13 September 2012

ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል መለስ ዜናዊን ይተካሉ ብለን ለምን አልጠረጠርንም?



       

የቀጣዩ የጎልጉል ኦንላይን ጋዜጣ ዘገባ “ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል መለስ ዜናዊን ይተካሉ ብለን ለምን አልጠረጠርንም?” የሚለውን ጥያቄ ያነሳብዎታል። እናካፍልዎ። (ጎልጉል) ሟቹን ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊን ለመተካት የሚደረገው የውስጥ ለውስጥ ሽኩቻ ኢህአዴግ እንደሚለው “በቀላል ሽግግር” የሚቋጭ እንዳልሆነ የሚጠቁሙ መረጃዎች እየወጡ ነው። መለስን በወኪሏ ወ/ሮ ሱዛን ራይስ አማካይነት በአስከሬን ሽኝቱ ወቅት ያቆለጳጰሰችው አሜሪካ የስልጣን ሽግግሩ ላይ ያላትን የማያወላዳ አቋም ትዕዛዙን ባለመቀበል ከሚመጣው መዘዝ ጋር ማስታወቋም ተሰምቷል።
የጎልጉል የአዲስ አበባ ምንጮች ከኢህአዴግ ከፍተኛ ደጋፊዎችና የቅርብ ባለሃብቶች እንዳገኙት ገልጸው በላኩት መረጃ የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር እንዲተኩ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር የሆኑትን አቶ ደብረጽዮን ገ/ሚካኤልን በቅድሚያ እጩነት መያዛቸውን አመልክተዋል።
መረጃ አቀባዮቻችን ደብረጽዮን ለሹመቱ የታጩበትን ምክንያት ሲያስረዱ መነሻ ያደረጉት በህወሓት ክፍፍል ወቅት የነበራቸውን ልዩ ሚና በማስታወስ ነው። በበረሃው የሽምቅ ውጊያ ወቅት የህወሓትን የሬዲዮ ማሰራጫ ጣቢያ በማቀናበር የሚታወቁት አቶ ደብረጽዮን አቶ መለስን በቅርብ እንደሚዛመዱና ለመለስ ቁልፍ ተግባራትን የሚያከናውኑ ሰው
እንደነበሩ የመረጃው ባለቤቶች በዝርዝር ተናግረዋል።
በዘመነ ህንፍሽፍሽ ህወሓት ለሁለት መሰንጠቁ ይፋ ከመሆኑ በፊት ልዩነቱ ውስጥ ውስጡን በተጋጋመበት ወቅት አቶ ደብረጽዮን ከአቶ መለስ የተቀበሉትን ልዩ ተልዕኮ ለመተግበር ያስችላቸው ዘንድ የሽሬ ምክትል አስተዳዳሪ ተደርገው ተሹመው ነበር። አፈንጋጭ የተባለውን ቡድን ከሚመሩት መካከል ዋና ኃይል አላቸው ተብለው የሚፈሩት አቶ ስዬ በትውልድ መንደራቸው ተምቤን ውስጥ ያላቸውን ሰንሰለት ለመበጣጠስና ለማምከን ልዩ ተልዕኮ ይዘው ወደ ሽሬ ያመሩት ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል ሃላፊነታቸውን በመወጣት ለመለስ አሸናፊነት ጉልህ ሚና መጫወታቸውን ምንጮቹ አመልክተዋል።

አቶ ደብረጽዮን በወቅቱ የሽሬ ምክትል አስተዳዳሪ ሆነው ሲላኩ “መለስን ስለሚቀናቀኑ አርቀው አሰሩዋቸው” ተብሎ በአባላቱን ዘንድ ይወራ እንደነበር ያስታወሱት የዜናው አቀባዮች አቶ መለስን በአገር ክህደት በመወንጀል ሊያስወግዳቸው የተነሳው የእነ አቶ ስዬ “ውህዳን” ኃይል በተሸናፊነት ከድርጅቱ በመባረርና በሙስና ወንጀል እስር ቤት እንዲወርዱ ከተደረገ በኋላ ዶ/ር ደብረጽዮን የተባረሩትን ከተኩት መካከል አንዱ ሆነው የህወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ተደርገዋል።
በሚኒስትር ማዕረግ ታላቁን የኢህአዴግ የስለላ መረብ ኢንሳን እንዲመሩ፣ ቴሌንም በቦርድ ሰብሳቢነት እንዲቆጣጠሩ ተሰይመዋል። ከዚህም በላይ ከፍተኛ የደህንነት ኦፕሬሽኖችን በዋናነት እንደሚመሩ ስለሚታወቅ በተቀጽላ ፓርቲዎቹ አመራሮችና በካድሬዎች ዘንድ ይፈራሉ። አቶ ደብረጽዮን ከአቶ መለስ ጋር ያላቸው ቁልፍ ግንኙነትና ተልዕኮ የጠነከረ ስለነበር በህወሃትና በተቀጽላዎቹ አጋፋሪ ፓርቲዎች ውስጥ በአመራር ላይ ያሉ አፍቃሪ መለስ ካድሬዎች በኩል ደብረጽዮንን የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የማድረጉ ሩጫ መነሻው የኋላ የታማኝነት ውለታቸው ሲሆን በሌላ በኩል የመለስ “ይተካኝ
የሚል እውነተኛው ኑዛዜ” ሊሆን እንደሚችል ምንጮቹ ግምታቸውን አኑረዋል። ከምንጮቹ በተጨማሪ የኢህአዴግ ማዕከላዊ ኮሚቴ ነሀሴ 30 ቀን 2004 ዓ ም ያካሄደውን ስብሰባ ያወጀው የመንግስት
ልሳን ቴሌቪዥን ስለ ተተኪው የድርጅቱ ሊቀመንበርና ጠቅላይ ሚኒስትር ሲያወራ አቶ ደብረጽዮን አስተያየት ሲሰጡ፣ በፈገግታ የተሞሉበትን ምስል በተደጋጋሚ ሲያሳይ ነበር። አቶ በረከትን ከአንድ ዳር የፊት ወንበር በትዝብት ሲመለከቱ የዘገበው የኢቲቪ ዜና፣ አዲሱን ሹመት “እጅግ ቀላል” በማለት በመጪው መስከረም በሚካሄድ የድርጅቱ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እንደሚያፀድቀው ከማስታወቅ ሌላ የዘረዘረው ነገር የለም። ስብሰባውን የመሩት የፓርቲው ምክትል ሊቀመንበር “ጓድ” ኃይለማርያም ደሳለኝ ነበሩ።
የስብሰባውን ውጤት አስመልክቶ ኢህአዴግ ያሰራጨውን ዜና በተመለከተ ያነጋገርናቸው የአዲስ አበባ ምንጮች አቶ ኃይለማርያም ከህወሓት በስተቀር በጠቅላላው የኢህአዴግ አቻ ድርጅቶች ዘንድ ሙሉ ድጋፍ ማግኘታቸውን አረጋግጠውልናል። በተለይም ኦህዴድ በቀጣዩ ምርጫ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ቦታ ለመረከብ ያስችለው ዘንድ ዛሬ ለአቶ ኃይለማርያም ስልጣን በማስረከብ በኩል ቀጥተኛ ድጋፍ እየሰጠ እንደሆነ ያመለከቱት ምንጮች በሌላ በኩል ደግሞ አቶ ደብረ ጽዮን የኦህዴድ ስራ አስፈጻሚዎችን ማነጋገራቸውንም ገልጸዋል። ከውሱን የብአዴን አመራሮች በስተቀር ህወሓት
የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ቦታ መልሶ እንዲረከብ ፍላጎት እንደሌላቸው ምንጮቻችን ጨምረው አስታውቀዋል። ደኢህዴን በበኩሉ የፓርቲው መሪ አቶ ኃይለማርያም ተጠባባቂ ጠ/ሚኒስትር ሆነው ሳለ፤ “ምክትል” እየተባሉ እንዲጠሩ መደረጉ ቅሬታ የፈጠረባቸው መሆኑን አባላቱ ውስጥ ውስጡን እየመከሩበት እንደሆነ የገለጹት የጎልጉል የክልሉ ምንጮች፤ አቶ ኃይለማርያምን በቀድሞው ሃላፊነታቸው ለማስቀጠል መሞከር ጸብ ሊያስነሳ እንደሚችል የደህንነቱ ክፍል መረጃ ማሰባሰቡን አስረድተዋል።
አቶ ኃይለማርያም አቶ መለስ ሲሰሩት የነበረውን ስራ ሁሉ የሚሰሩ ተጠባባቂ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆናቸውን፣ፓርላማው ስርዓት ለማሟላት ሲባል ሹመታቸውን እንደሚያጸድቀው አቶ በረከት ካስታወቁ በኋላ እርሳቸው የሚመሩት የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ድርጅት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝን “ምክትል” በማለት መጥራቱ ክብራቸውን መንካት እንደሆነም ተመልክቷል። አቶ መለስ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ግልጽ ሆኖ ሳለ ለአጭር ጊዜ ከሥልጣናቸው የተለዩ ይመስል አቶ ኃይለማርያምን “ምክትል” እያሉ መጥራት በሕግ የሚያስጠይቅ ሊሆን ይገባዋል የሚሉ ወገኖችም እየተበራከቱ መጥተዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ይህ ሕገወጥ ድርጊት ሕገመንግሥቱ ምን ያህል ክፍተት እንዳለው የሚያመላክትና አቶ መለስም ምን ያህል ነገሮችን ቆላልፈው ያለገደብ ይገዙ እንደነበር በግልጽ የሚያሳይ ነው ሲሉም
ይከራከራሉ፡፡ ይህም ስለሆነ ነገ አቶ ኃይለማርያም ሥልጣኑን ከነሙሉ ኃላፊነቱ ከተረከቡ ህወሓት በተቆጣጠራቸው የጦር ኃይል፣ የደኅንነት፣ ወዘተ ቦታዎች ላይ ሊወስዱ የሚችሉት የማመጣጠን ሥራ ህወሓትን ከወዲሁ ስላስፈራው ነው የሥልጣን ሽግግሩ ጊዜ የፈጀው በማለት ከአገር ውስጥ የሚመጡ አስተያየቶች ይጠቁማሉ፡፡  በተመሳሳይ ዜና የስልጣን ግብግቡ ያላማራት አሜሪካ ቀጭና ትዕዛዝ ማስተላለፏን የጎልጉል የዲፕሎማት ምንጮች አስታወቁ። ምንጮቹ እንዳሉት አሜሪካ በህገመንግስቱ መሰረት አቶ ኃይለማርያም የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ቦታ ካልያዙ የአሜሪካን ጥቅምና ትዕዛዝ ባለማክበር የሚከተለውንም መዘዝ አሜሪካ አስቀድማ ይፋ አድርጋለች።
“የህወሓት ሰዎች ስልጣኑ ከእጃችን አይወጣም ካሉ ምን ሊከተል ይችላል?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ አንድ ስማቸውን እንዳይጠቀስ የጠየቁ ከፍተኛ ባለስልጣን “የሚያገኙት ርዳታ ይቆማል፤ የህወሓት አባላት ላይ የበረራ ጉዞ እቀባ ይደረግባቸዋል፤ ሌሎችም ተመሳሳይ ርምጃዎች ይወሰዳሉ” በማለት አጭር መልስ ሰጥተዋል። በኬኒያ ከምርጫ ጋር በተያያዘ ተከስቶ በነበረው የጎሳ ግጭትና ዘር ማጥፋት ተሳትፎ በነበራቸው አስር የፓርላማ አባላት ላይ አሜሪካ ተመሳሳይ እርምጃ መውሰዷ የሚታወስ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከጎልጉል ጋር ቃለ ምልልስ ያካሄዱ “አብዮታዊ ዴሞክራት” (ዝርዝሩን በ “እናውጋ” ዓምድ ይመልከቱ) እንደተናገሩት ኢህአዴግ ካሁን በኋላ በህወሓት የበላይነት የሚመራበት ጊዜ ሊያከትም እንደሚችል ተናግረዋል። መለስ የቆፈሩት ጉድጓድ ትልቅና አፉን ከፍቶ የሚውጠውን እየጠበቀ እንደሆነ ያስታወሱት እኒሁ የኢህአዴግ ሰው “እስከዛሬ ተታለሃል” የሚለው የኅሊና ወቀሳና፣ ለሁሉም ድርጅቶች የጋራ ነጥብ የነበሩት አቶ መለስ መሞታቸው ተዳምሮ አመራሩን ለመውስድ ከያቅጣጫው ጥያቄ መነሳቱ የማይቀር እንደሆነ ልምዳቸውን በማካተት ተናግረዋል።
(በጎልጉል ሪፖርተር)

No comments:

Post a Comment