"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Friday 7 December 2012

የሹም-ሽሩ ምስጢርና ዋናው ጠቅላይ ሚኒስትር!



በሰሎሞን ተሰማ ጂ. (semnaworeq.blogspot.com)

ባለፈው ሐሙስ በተደረገው የኢህአዴግ/ወያኔ የካቢኔ ሹም-ሽር ላይ በርካታ አስተያየቶች በመደመጥ ላይ ናቸው፡፡ ሆኖም የበርካቶቹ አስተያየትና ትንተና እዚህ ግባ የማይባልና፣ በወያኔዎች አማርኛም “ውኃ የማይቋጥር” ሆኖ ስላገኘሁት፣ የኔን አስተውህሎት ላቀርብ ወደድኩ፡፡ በቅድሚያ ግን፣ በሀገር ውስጥ ያሉት የተቃዋሚ ፖለቲካ ማኅበሮች/ፓርቲዎች መሪዎች እየተቀባበሉ የሚደጋግሙት ነገር ያው የተለመደውን ነው፤ “ሹመቱ ሕገ መንግሥቱን የተከተለ አይደለም!” ምናምን የሚል ወቀሳ አይሉት ትችት፣ እንዲያው የንፉግና የፈሪ ጩኸት ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎቹን መሪዎች ወያኔ ደጋግሞ አጥጋቢ አማራጭ የላችሁም የሚላቸው ለምን እንደሆነ፣ ብዙዎቹ አሁንም አልተገለጠላቸውም፡፡ መቼ “ተገለጠ/ቡድሀ!” ብለው እንደሚጮሁ አላውቅም፤ በተስፋ ግን እንጠባበቃለን፡፡



ወደዋናው ጉዳያችን እንመለስ፡፡ ኢሕአዴግ/ወያኔ የሰሞኑን ሹም-ሽር ሲያደርግ ለሕዝቡ አዲስ ነገር አልሆነበትም፡፡ አዲስ ነገር የሆነባቸው ካሉም ኢሳት ቴሌቪዥን በነሐሴ 2004 ዓ.ም ያወጣውን መረጃ ያላነበቡትና ወቅታዊ የፖለቲካ ጥንቅሮችን የማይከታተሉት ወገኖች ብቻ ናቸው፡፡ በሀገር ጉዳይ (በወል ቤታችን ጉዳይ ላይ እስከመቼ ድረስ ቸልተኛና ገለልተኛ ሆነው እንደሚቀጥሉ ባይገባኝም) ላይ ቸለል የሚሉት ወገኖች ናቸው፡፡ ከዚያ ወጭ ያሉትና የወቅቱን የሕወሀት-ወያኔን መቅነዝነዝ ሰበብ ያልተረዱት ብቻ ናቸው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የአቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ነፍስ ፖለቲከኛ ሆና በመገኘት ፈንታ “መሲሐዊት” ለመሆን እየተንደፋደፈች መሆኗን ወያኔዎች መረዳታቸው ነው፡፡ በመሆኑም ከነበሯቸው ብዙ ብዙ አማራጮች መካከል የሦስት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮችን ሹመት አጸደቁ፡፡

የፓርላማውን ስርጭት ለተመለከተው ሰው ሁለት የሚደንቁ አልቦ-ቋንቋ እንቅስቃሳችን ጠቅላይ ሚኒስትሩና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን አሳይተዋል፡፡ የተሹዋሚዎቹን ስም ዝርዝር ሲያነብ የነበረው ኃይለ ማርያም ደሳለኝ (The Mimic Man)፣ መለሰ ዜናዊኛ ማስኩ/ጭንብሉ ጠፍቶበት ሲኮለታተፍ ነበር፡፡ ምናልባትም በሥራ ብዛት ሰበብ ይህንን የሚያህል ድርጅታዊ ውሳኔ ሲወሰን በስብሰባ ላይ አልተገኘም ነበር ይሆናል፡፡ ጎበዞቹ የወያኔ አርክቴክቶች ውሳኔያቸውን እንዲያነብ አዳራሹ ውስጥ ከገባ በኋላ ነው የሰጡት፡፡ የተሹዋሚዎቹን ስም ዝርዝር ሲያነብ ከፍተኛ የሆነ ቃና-ቢስነት ይታይበት ነበር፡፡


ተሹዋሚዎቹ ቃለ መኻላቸውን ከፈፀሙ በኋላ ደግሞ አቶ ደመቀ መኮንን ፊቱን አቀጭሞ ለማጨብጨብ እንኳን ሲጠየፍ ላየው፣ በሥራ ብዛት የተነሳ፣ እርሱም ይህንን ከፍተኛ ድርጅታዊ ውሳኔ ሳይሰማ እንደቀረ ያጋፍጣል፡፡ ያም ሆኖ፣ ከ1998 ዓ.ም ጀምሮ በእኩልነት ላይ ያልቆመው የኢሕአዴግ/ወያኔ ካቢኔ በስመ ክላስተር፣ ቀደም ብሎ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አዲሱ ለገሰ አስይዞት የነበረውን የግብርናና ገጠር ልማት ኃላፊነት ሸርሽሮ ልፍስፍስ ክላስተር አደረገው፡፡ በአቅም ግንባታው ሚ/ር ተፈራ ዋልዋ ተይዞ የነበረውን ሸርሽሮ ለአቶ ሙክታር ሰጠው፡፡ በዶ/ር ካሱ ኢላላም ተይዞ የነበረውን የመሠረተ ልማት ሚኒስትርነት ሥልጣን አዘምኖና ደራርቦ፣ በዚያም ላይ የቴሌኮሙን ደሕንነት ከነማዕከላዊው ደሕንነት ተያያዥ ኃላፊነቶች ለዶ/ር ደብረ ፂዮን ሰጠው፡፡ እንደተለመደው፣ ከፈረንጆቹ ጋር የመሞዳሞዱን ጉዳይ ለይስሙላ ለኃይለ ማርያም ሰጥተው ሲያመነቱ ከቆዩ በኋላ፣ መልሰው “በስዩም መስፍን ርስት፣ ዶ/ር ቴድሮስ አድኀኖም ሆይ-ግባበት!” አሉት፡፡

የሹምሽሩ ፖለቲካዊ አንደምታዎች ምንድናቸው?

ዋነኛውና የመጀመሪያው ነጥብ የአቶ ኃይለ ማርያም ባሕሪ ከተሞክሮ መታወቁ ነው፡፡ በ1993ዓ.ም በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በኃላፊነት ሲሠራ ሳለ መጠነኛ የተማሪዎች ነውጥና ግርግር ሲፈጠር፣ መቆጣጠር ተስኖት ወደሃይማኖታዊነቱ አዘነበለ፡፡ መራሹ ወያኔም፣ በራሱ መንገድ የተማሪዎቹን አመጽ መረሸው፡፡ ከአባተ ኪሾም ቀጥሎ በደቡብ ክልል ርእሰ መስተዳድርነት እየሠራ ሳለ፣ የሲዳማዎችና የከንባታዎች አመጽ ሲነሳ፣ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ እንደተለመደው መቆጣጠር ተስኖት መልቀቂያ ሁሉ ሊያስገባ እያመነታ እንደነበር የቅርብ ሰዎቹ ይመሰክራሉ፡፡ በ1998 ዓ.ም በኋላም ቢሆን የሚያስጨንቁ ችግሮች ሲከሰቱ መውጫ ቀዳዳ የሚፈልገውን ኃይለ ማርያም፣ አቶ መለሠ ዜናዊ እንዴት mimic man መሆን እንደሚችል እያረሳሳ ነበር ያቆየው፡፡ ስለዚህም፣ አቶ ኃይለ ማርያም የኋሊት የፈረጠጠ እንደሆ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱ ሥልጣን በታሪክ አጋጣሚ ኃይለ ማርያም ላይ እንደወደቀው ሁሉ፣ “ደግሞ አቶ ደመቀ መኮንን እጅ ሊወድቅ አይደለምን?” ብሎ ያልሰጋ የወያኔ ከፍተኛ አመራር አልነበረም፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትርነቱ ሥልጣንም በአቶ ደመቀ መኮንን እጅም እንዳይወድቅ የማይፈልግበት ሁለት ምክንያቶች አሉ፡፡ አንደኛው ምክንያት የዘሩ ጉዳይ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ የሃይማኖቱ ጣጣ ነው፡፡ ሁለቱንም ነጥቦች ለጥቆማ ያህል እናንሳቸው እንጂ በዝርዝር እንዳናስቀምጣቸው እንፈልጋለን፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ለወያኔ አጀንዳ መመቸት ስለሚሆን ነው፡፡ ለማንኛውም፣ የአቶ ደመቀ መኮንን አሊን ምርጫ፣ በሁለቱ መሥፈርቶች ምክንያት አደገኛ የሆነ ችግር እንደሚያስከትል በዝግ የወያኔ ስብሰባዎች ላይ ተደጋግሞ ተወሳ፡፡ በመጨረሻም፣ ሦስት የመጠባበቂያ እቅዶች ተነደፉ፡፡ አንደኛ፣ በውስጥ የስልጣን ውክልና የሚብላላውን ኦሕዲድን ለማስተንፈስ አቶ ሙክታርን በምክትል ጠ/ሚኒስትርነት ማዕረግ ለመሾም፤ ሁለተኛ፣ አቶ ደብረ ፂዮንን በፊታውራሪነት አስቀድሞ፣ የአቶ ኃይለ ማርያም ባሕሪያዊ ችግር ቢፈጠር እንዲተካው ማዘጋጀት፤ እና ሦስተኛም፣ ምናልባት ደብረ ፂዮንን ሕዝቡ ባይደግፈው/If not Popular/፣ ከአቶ አርከበ እቁባይ ቀጥሎ ሕዝባዊ አመኔታ እያገኘ ያለውን ቴድሮስ አድኃኖምን በመጠባበቂያ ዕቅድነት ይዞ መንቀሳቀስ የሚሉ ነበሩ፡፡

ስለሆነም የሹም ሽሩ ዋነኛው አንደምታም፤ ምናልባት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በርትቶ ኃላፊነቱን ከተወጣ እሰየው፤ ካልተወጣ ግን በነሐሴ 2004 እና በመስከረም 2005 ዓ.ም፣ በድሕረ-መለሠ ዜናዊ ወቅት የተፈጠረውን የሕወሀት-ወያኔ የተተኪ መሪዎች ችግር ለመፍታት ነው፡፡ በመሆኑም፣ ሦስቱ የወያኔ እህት ድርጅቶች አንድ አንድ እጩዎችን ሲያዘጋጁ (ለዚያውም የፖለቲካ ውሳኔዎቻቸውና የሥልጣን ምሕዳራቸው ልፍስፍስ በመሆኑ የተነሳ አፈጻጸማቸው ደካማ እንዲሆን ሆን ተብሎ ተዘይዷል)፣ ሕወሀት-ወያኔ ግን ሁለት እጩዎችን አዘጋጅታለች፡፡ ለዚያውም በጉልሕ ሙሉ ሥልጣናቸውና አፈጻጸማቸው ሳይቀር እንዳይስተጓጎል ተብሎ የፋይናንስና የኤኮኖሚውን ክላስተር ከነደሕንነቱ፣ ከነውጭ ጉዳይ ጽ/ቤቱ፣ ብሎም ከነመከላከያ ሠራዊቱ ይዘው እንዴት አፈጻጸማቸውና ሥልጣናቸው ሊቀጥል አይችልም?

እንግዲህ ወደማጠቃለያ ሀሳባችን ተዳርሰናል፡፡ እንደምታስታውሱት ኢሕአዴግ የአራት ድርጅቶች ጥምር ፓርቲ ነው፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ሥልጣን እስካሁን ሦስት ፓርቲዎች ተቋድሰውታል፡፡ ኢሕዴን/ብአዴንን ወክሎ አቶ ታምራት ላይኔ ከሰኔ 1983 ዓ.ም እስከ መስከረም 1987 ዓ.ም ድረስ ጠቅላይ ሚኒስትር ነበር፡፡ ከ1987 መስከረም ወር ጀምሮ እስከ ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም አቶ መለሠ ዜናዊ ሕወሀት/ወያኔን ወክሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ነበር፡፡ አሁን ከመስከረም 9 ቀን 2005 ጀምሮ ደግሞ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ደሕዴድን ጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ተረክቧል፡፡ ሁሉም ነገር በተያዘለት መርሀ ግብር መሠረት ከሄደም፣ ቀጣዩ የወር ተረኛና ጠቅላይ ሚኒስትር ከኦህዴድ መሆን ይኖርበታል፡፡ ነገር ግን፣ የአማሮችና የኦሮሞዎች ጠቅላይ ሚኒስትርነት የማይዋጥለት የወያኔ ከፍተኛ አመራር መልሶ ለመጠቅለል የሚያስችለውን የማሳሳቻ /camouflage/ ዕቅድ ነድፏል፡፡ በዚህም እቅድ መሠረት፣ ሕወሀት-ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር ከደቡብ እንዳይሆን ለመከራከር ከመሞከሩም በላይ፣ እድሉን ክፍ አድርጎ ለመገኘት ሲል በሁለት እጅ ብልጫውን ለመውሰድም ተዘጋጅቷል፡፡ ኦሕዲድ በሙክታር ሊወከል ቢችልም ቅሉ፣ መስከረም 2005 ላይ ሱፊያን አሕመድ የገጠመውን ጽዋ ይጎነጭ ይሆናል፡፡ አቶ ደመቀ መኮንንም ልክ እንደቀዳሚዎቹ የብአዴን ም/ጠቅላይ ሚኒስትሮች አቶ ተፈራ ዋልዋና አቶ አዲሱ ለገሰ ዓይነት “እርም ጠቅላይ ሚኒስትርነት!” ብሎ ይቀራል ማለት ነው፡፡ በማካያውም፣ ሕውሀት በዶ/ር ደብረ ፂዮንና በዶ/ር ቴድሮስ አድኃኖም አማካይነት ከብአዲንና ከኦሕዲድ ተወካዮች ጋር ሲወዳደሩ ሃምሳ-በመቶ (50%) እድል ይኖራቸዋል ማለት ነው፡፡ ይህንን እድል ማን ይሠጣል? ደንበኛ የማሳሳቻ /camouflage/ ዕቅድ ነድፏል ማለት እንዲህ ነው፡፡ (ቸር እንሰንብት!)

No comments:

Post a Comment