"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Thursday 10 January 2013

ጀግናን መግደል ይቁም

ጀግናን መግደል ይቁም
ከሳሙኤል ሽፈራው፣ ከዳላስ
CNN HEROES, በ2007 እ ኤ አ ጀምሮ በአለማችን ለሰውልጆች መልካም አሳቢና አድራጊ ናቸው የሚባሉ ግለሰቦችን በመፈለግ ለመልካም ተግባራቸው አለማቀፍ እውቅና እንዲያገኙና ለመልካም ተግባራቸው ምስጋና ይሆን ዘንድ በአንደርሰን ኩፐር በአመት አንድ ጊዜ የሚዘጋጅ የምርጫ ቀን ነው። መልካም ስራ ያከናወኑ በዚህ ቀን የሰሩት ተግባራት ለአለም በCNN ኔትወርክ ቀርቦ ከመሃላቸው በላጭ ተግባር ላደረገ ተገቢ ሽልማት ይሰጠዋል። ጀግናን ማወደስ ለአሜሪካኖች አዲስ ነገር አይደለም። ለእኛ ትንሽ ብለን ለምናስበው ተግባር የፈጸመን ሰው የጀግና ስም ይሰጠዋል። ለስራውም ሙሉ ምስጋና ያገኛል። አንዳንዴ ግለሰቦች እረ የሰራሁት ጀግና አያሰኘኝም እስኪሉ ተገቢውን ከበሬታ በህብረተሰቡ ይለገሳቸዋል። እናም ይህን ያየ ሁሉ በክፉ አጋጣሚና ጊዜ ዜጋን ለመርዳት ወደኋላ አይልም። አንዳንዴ እውነትም አስገራሚ የሆኑ ተግባራትን የሚያከናውኑ ብዙ ናቸው። ይህ ደግ ባህል ነው። ጀግናን ማሞገስ ተገቢ ነው። ክፉ ቀን ሲመጣ አለሁ የሚል ይገኛል። ለወገን ለአገር ለመቆም፤ አስፈላጊውን መስዋእትነት ለመክፈል አቅም ያለው ሁሉ ዝግጁ ይሆናል።
ጀግንነትና መስዋእትነት በዛሬይቱ ኢትዮጵያ
እንዴው ከመቶ አመታት በፊትና የአገራችን የተፈጥሮ አቀማመጥና የከባቢ ፖለቲካ ያስከተለውን ከትውልድ ወደ ትውልድ ነቅተን እንድንጠብቅ ያደረገንን ትተን፤ ላለፉት 60 እና 70 አመታት የተከሰተውን የባህልና የአስተሳሰብ ለውጥን መመልከቱ በቂ ግንዛቤ የሚሰጠን ይመስለኛል። ከታየው ባህላዊና ስነልቦናዊ ለውጦች አንዱ፤ ለሕዝባችን አዲስና ባእድ የሆነ፤ ጀግናን የመግደልና ፈሪን የማንገስ የማወደስ ባህል የመጣው በነዚሁ አመታት፤ በተለየም ከጠላት ወረራ ወዲህ በመሆኑ። ለዚህ ስነልቦናዊ ለውጥ ምክንያቶችን መመልከቱ በቂ ግንዛቤ ይሰጠናል። ይህን የኔን ሀሳብ የማይቀበል ሰው የራሱን ቢያቀርብ ከውይይት መልካም ግንዛቤ ሊገኝ ይችላል።
ኢትዮጵያ ሐገሬ ሞኝ ነሽ ተላላ፣
የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ።
አገራችን እጹብ ድንቅ ያሰኙ ጀግኖች የተፈጠሩባት አገር ናት። እንዴው የረጅሙን ዘመን ታሪክና የአገር አውራ ጠባቂወችን ትተን፤ ከቅርቡ የሁለተኛው አለም ጦርነት ብለው አውሮፓውያን ከሚጠሩት መባቻ ጀምረን ይህችን አገር አሳልፎ ላለመስጠት ሲሉ ህይወታቸውን አሳልፈው የሰጡትን ቆጥረን የምንዘልቀው አይሆንም። እናም በዚያ አርበኛ ትውልድ የተካውም ቢሆን እንደነሱ ለአገሩ ከልክ ያለፈ ፍቅር የነበረውና የነዚያ ያርበኛ ትውልድ ልጆች ነበሩ የየካቲቱን የለውጥ ትግል ያቀጣጠሉት። ለውጡን ከነጣቂ ለማስቀረት ሲሉም በየጎዳናው በጥይት የተረፈረፉት። ታዲያ እንደዚያ ያሉ ጀግና ትውልዶች ያለፉባት አገራችን ለምንና እንዴት ተቃራኒ ባህልን ማስተናገድ ተቻላት? ይህ አዲስ ጀግና አራካሽና ፈሪ አወዳሽ ባህልን ከመስፋፋቱ በፊት በነበረው ጊዜ ለግምት በሚያስቸግር አያት ቅድም አያቶቻችን ነጻነታችንን በተጋድሎና በመስዋእትነት ጠብቀው አቆዩን።በቀደመውም ጊዜ ላገር መሰዋት ክብር ነበርና፤ ዜጎች የአርበኛን ገድል በዘፈንና አፍ ለአፍ በሚተላለፍ ታሪክ አቆዩን።
በሻህ ቢሰዋ ተተካ ባልቻ
መድፍ አገላባጭ ብሻ ለብቻ፡
ይህ ከላይ ያስቀመጥሁት በአደዋ ጦርነት ከዳግማዊ አፄ ሚኒሊክ ጋር የዘመቱት በሻህ አቡዬ በጀግንነት ሲሰው፤ ባልቻ አባነፍሶ ተክተው ጀግንነቱን ሸፈኑ ለማለት የተቀኘ የፉከራ ስንኝ ነበር።
ተሰቀለ ቢሉኝ፤ ጀበርናው ነው ብየ
ተሰቀለ ቢሉን ዝናሩ ነው ብየ
ለካስ በላይ ኖሯል ትልቁ ሰውየ
ይህ ደግሞ በበገናና በክራር አንጎራጓሪ የደረደረው የሐዘን እንጉር ጉሮ ነው። ይህን ከላይኛው የሚለየው አንዱ በጀግንነት በጦር ሜዳ የተሰዋ ሲሆን። ሌላው ጠላትን ያርበተበተና እግዞ ያሰኘ ጀግና በራሱ ወገን በፈሪ ስብስብ የተፈረደበት ጀግና ነው።
ጀግና የመግደል፤ የማዋረድና፤ ፈሪን፤ ፈርጣጭን የማወደስ ታሪካችንም የጀመረው ከሁለተኛው የጠላት ወረራ በኋላ ይማስለኛል። ስለአገራችን ጀግኖች፤ ለትውልድ ይደርስ ዘንድ ብዙ ያለፉም አሁንም በሕይወት ያሉ ታላላቆቻችን በመጽሀፍ አቅርበውልናል። በቅርቡም በአቶ ዘውዴ እረታ የቀረበው የቀዳማዊ ሐይለስላሴ ንግሰ ታሪክ አንዱና ሊነበብ የሚገባው ነው። ከመሐላችን ያሉትን ዘውዴ እረታን እድሜ ከጤና ጨምሮ ይስጥልንና መጭ ትውልዶች እንዲደርሳቸው ብዙ ታላላቅ ታሪካዊ ስራወቻቸውን አካፍለውናል።
እናም ከታሪክ እንደምንረዳው አገራችን ህልቆ መሳፍርት የሌላቸው አያሌ ሰማእታት ነበሯት፣ አሁንም አሏት። ሆኖም ካለፉት ታሪክ ለመማር ቀርቶ ዛሬ ዛሬ እንድናወድስ በሰፊው እየተገደድን ያለው ፈሪንና ክፉ አድራጊን ሆኗል። የጀግና ስምን ማንሳት የፋሮች፣ ነውና ውግዝ ከማሪወስ ይባላል። በቅርብ ታሪካችን እንኳን ብንነሳ እንደ ዶክተር ታየ ወልደሰማያት አይነት አንበሳ የዚህች አገር ልጆች ዛሬ የት ደረሱ? ብለን ብንጠይቅ መልሱ ጠላት ያልሰበረውን ስነልቦናቸውን፤ ጠላትን እቃወማለሁ የሚል ዛርጢ አንገብግቦ እንዲሰወሩ አደረጋቸው ብል ስህተት አይመስለኝም።፡አንድ ሰው ለሰራው ስራ። ለከፈለው መስዋእትነት ምላሹ የስም ማጉደፍ ዘመቻ ከሆነ፤ ሌላው እንዴት የዚያን እግር ተከትሎ እንቢ ለሀገሬ እንቢ ለሕዝቤ ነጻነት ብሎ በልበ ሙሉነት ሊነሳሳ ይችላል? ለዚህም መልሱ ያው አንገት መድፋት የሚያስከትልን ነገር መራቅና አርፎ መቀመጥን መምረጥ፡ዛሬ የብዙ አያሌ ጀግኖቻችን እጣ ፈንታ ሆኗል።
ድሮ የዚያ የአብዮታዊ የንቢ ባይ ትውልድ ሲነሳሳ ፋና አድርጎ የተነሳው አገራችን በጠላት ስትወረር በዱር በገደሉ ተሰደው መላ አለም በተለየም የሰለጠነው አለም አለቀላቸው ብሎ በአንድ አብሮና ተባብሮ በነሱ አንጻር ሲቆም፣ መሳፍንትና መኳንንት አለቀልን ብለው አገር ለቀው ሲሰደዱ፤ ስም ያልነበራቸውና የማይታወቁ ገበሬወች ናቸው
ሞፈሬን ቀንበሬን ሰጠሁት ለሌላ
አገሩ ለሚኖር ሰርቶ ለሚበላ።
እልም ነው፤ ጭልጥ ነው እውሀ አይላመጥም
ጠላት ወዳጅ ላይሆን አልለማመጥም።
በማለት ዱር ቤቴ ብለው የነበራቸውን ጋሻና ጦር ከፍ ሲል ደግሚ አንድ ጎራሽ መውዜር አንጠልጥለው ጫካ የገቡት። እነዚያ ጀግኖች በሽሬ በራስ እምሩ በሚመሩት ሰራዊት። በማይጮ በራስ ሙሉጌታ ይገዙና በሰራዊቶቻቸው። በደቡብ በራስ ደስታ ዳምጠው የተከፈለውን መስዋእትነት ፋና ወጊ አድረገው እንጅ፡ ቦዶሊዮ አዲስ አበባ ከመግባቱ በፊት የምን አገር ማዳን ብለው የተሰደዱትን ተመልክተው አልነበረም።
ዛሬ ላይ ሆነን ያንን ስንመለከት (ስንዘክር) ጀግንነት የፋራነው በሚያሰኝ የአፍ ጀግኖችንና ጀግና ገዳዮችን አንግሰን እንገኛለን።
በቅርቡ የወያኔው ቁንጮ አንገት ያስደፋውን የአበበ ገላውን ቪዲዮ አይቸ መጥገብ አልቻልሁም። ቁጭ ብየ ስተክዝ ሁል ጊዜ የሚታወሰኝ የዘርአይ ደረስ በጣሊያን ዋና ከተማ የአከናወነው የጀግንነት ታሪክ ነው። እናም አበበ እንደዚያ ይመሰልብኛል። በአንጻሩ በእርግጠኝነት ይህን ጀግና እንደ ታየ ወልደሰማያት ለማብጠልጠል የሚሸርቡ ጀግና ገዳዮች እንዳሉ ሲታሰበኝ፡ይዘገንነኛል። ምክንያቱም ላለፉት አራት አስርት አመታት ያለፉ ጀግኖችን ስም ሲወደሱ ሳይሆን፣ ዘርና አጥንታቸው እየተቆጠረ ልክ እንደወያኔው ዘረኛ ቡድን ሲብጠለጠሉ ተመልክቻለሁና ነው። ገርማሜንና መንግስቱ ነዋይን፤ ወይንም ወርቅነክ ገበየሁንና ጽጌ ዲቡን ዛሬ የሚያነሳ የሚያወድስ የለም። ተስፋየ ደበሳይን፣ ግርማቸው ለማን ወይንም ውብሸት ፍስሀና ጽገየ ገ/መድሕን (ደብተራው) እና በአዲስ አበባ ዘመን ከሰጠው ጠባብ ቡድን ጋር 1994 ዓም በቀን ተታኩሶ የወደቀውን ጋይምን የሚያነሳ የሚያወድስ ወይንም ፈለጋቸውን ለመከተል የሚፎክር ባለማየቴ ነው።
በዚህ በተነሳሁበት እርእስ ብዙ ማለት ይቻላል። ከጠላት ወረራ ጊዜ ጀምሮ ያገራቸው አፈር በልቷቸው የቀሩ ለዝክረ ሰማእትነት እድሉ የተነፈጋቸው ብዙ ናቸው። ከላይ እንዴው ለላሙና ያክል ምሳሌ እንዲሆነን እንጅ ሁሉን መጥቀስ ቢቻል እንዴት መልካም ነበር። ለዚህ መጥፎ ልማድ ያበቃን ሁለት ኩነቶች ባገራችን ተከናውነዋል። አንደኛውና ዋነኛው፤ ጣሊያን በጀግኖቻችን መስዋእትነትና ተጋድሎ አገር ለቆ ከወጣ በኋላ ሲሆን፤ ይኸውም አርበኛን ወደጎን አድርጎ ባንዳንና ስደተኛን መሾም መሸለም፤ አርበኛን ማግለልና ማናናቅ፤ ብሎም ለግዞትና እስራት መዳረግ ሲሆን። ለዚህ ቅድሚያውን የበላይ ዘለቀ ከሁለት ወንድሞቹ ጋር የደረሰባቸው የሞት እጣ ሲሆን፣ በቀጣዩ አመታት ገረሱ ዱኪ፤ ነጋሽ በዛብህ፣ መንገሻ ጀንበሬ፣ ኋላም ታከለ ወልደ ሐዋርያት በተዋደቁላት አገር በክብር አላለፉባትም።
ሁለተኛው ባህላዊ ለውጥ በወታደራዊ ደርግ የተከናወነ ሲሆን። ሕዝብን ስነልቦናውን ሰብሮ በአደባባይ ልጅን ገድሎ እሬሳን መሸጥ ብሎም ወላጅ አባትና እናት ልጆቻቸውን አልቅሰው በክብር እንዳይቀብሩ የተከለከለበት አዲስ ሁኔታ ነው። ያን አይነት በወገን በአገር ላይ የደረሰ የመንፈስ ጉዳት ለዛሬው አገርን ለአናሳ ጠባብ ብሄርተኛ አስረክቦ መቀመጥ ምክንያት ሆነ የሚል የግል እምነት አለኝ። ሁሉ ነገር ፖለቲካ ነው ብሎ መፈጸምና ክብርን አሳልፎ መስጠት ብልጠት እንጅ ጅልነት ያልሆነበት ጊዜ ላይ ነን። ለአገር ብለው የሚታገሉትን ማብጠልጠል፤ ማዋረድ እና ክብራቸውን መዳፈር አዋቂነት ነው። ይህ አድራጎት ይበልጥ እንዲስተጋባና ስር እንዲሰድ ዘመናዊው የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው አስተዋጽኦው የሚናቅ አይደለም። ፓልቶኮችና ድህረ ገጾች ሕዝብ አሰባሳቢና ቀስቃሽ የሆኑትን ያክል፤ከምኝታ ቤታቸው ጎድበው ስም ለሚያራክሱ ፈሪወችም አስተዋጸኦ አላቸው። ፓልቶክን ካነሳን ላይቀር በቅርቡ በቃሌ አስተዳዳሪወች የተጀመረው ለአገር አስተዋጸኦ ላደረጉት የምስጋና ፕሮግራም መጀመር እሰየው የሚያሰኝ ነዉና እንዲበረታቱና ቀጣይነት እንዲኖረው አበጃችሁ እላለሁ።
ሰሞነኛው የፈሪወች ዘመቻ
ለዚህ አጭር መጣጥፍ ያበቃኝ በዚህ ባሳለፍናቸው ሳምንታት በታሕሳስ ወር የመጨረሻ ያየኋቸው ናቸው። መጀመሪያ አቶ እያሱ አለማየሁ ለአንድ የራዲዮ ቃለ ምልልስ ቀርበው ግለሰቡን አስታከው የቀረቡ አስተያየቶችና ጥያቄወች ከፊሉ አንድን ትውልድ አውጋዥና የተከፈለን መስዋእትነት አራካሽ ሆነው አግኝቻቸዋለሁ። በእርግጥ ተገቢም የሆኑና መልስ የሚፈልጉ ጥያቄወች እንደነበሩበት ልክድ አልችልም። ሌላው በለንደን የሸንጎ ስብሰባ ተንተርሶ በትቂት ግለሰቦች በአቶ መርሻ ላይ የቀረቡ ዘለፋወች ናቸው። እናም የዚያ ትውልድ አካል እንደመሆኔ፤ አፍላ እድሜየን ለዴሞክራሲ ጥያቄን አንግበው ከተነሱት ጋር በኢሕአፓ ስር ሆኘ የታገልሁ የታሰርሁ የተንገላታሁን ከትውልዱ ተረፉ ከሚባሉት ትቂቶቹ አንዱ ነኝና ከላይ በጠቀስኳቸው ሁለቱ ግለሰቦች ላይ የተሰነዘረው መረን የለሽ ዝልፊያን መቀበል፤ የተከፈለን መስዋእትነት እንደመካድ ቆጥሬዋለሁ። ግለሰቦቹ በየቅል ሰው እንደሞሆናቸው ሊኖራቸው የሚችሉ ድክመቶች ቢኖሩ አስገራሚ ባይሆንም፤ የከፈሉት እና እየከፈሉት ያለን መስዋእትነት መካድ ብሎም ማብጠልጠሉ አግብነት የለውም። ከላይ እዳሳየሁት አዲሱ ባህል ፈሪን አንግሶና አወድሶ ጀግናን ማራከስ የሚጠቅም ሳይሆን ለትውልድ የሚተላለፍ ክፉ ደዌ ነውና መቆም አለበት። እናም በየትኛውም ሚዛን ከላይ የጠቀስኳቸው ግለሰቦች የጀግንነት መስፈሪያውን ያሟላሉና ነው።
እንዴው ለማለት ያክል ለመሆኑ ሙሉ እድሜን ለዚህ ትግል ብሎ ያሳለፈ ሰው ወይንም እያሳለፈ ያለ አለወይ? ዛሬ ይህን ከፋፋይ ጠባብ ቡድን ለመለወጥ በሚካሄደው ትግል አንደኛውና ዋነኛው ችግር እኮ የትርፍ ጊዜ (part-time) ታጋዮች መበራከት ነው። ታዲይስ አቶ መርሻን አይነት እና የዚያን ትውልድ መሪወች ማብጠልጠል ምኑ ነው የሚጠቅም? እስኪ አሁንም በኢሕአፓ ስር ካሉት አንድ ሁለት ተብለው ከሚቆጠሩት ውጭ ኑሮ ትግሌ ብሎ የሚኖር አመላክቱኝ። አወ የነሱን ፈለግ ተከትለው በየትም ይሁን በየት የሚንቀሳቀሱ ሊኖሩ ይችላሉ። ግን ቁጥራቸው 10 እና 20 ከደረስ እሰየው ያሰኛል። ይህ ማለት ለእውነት እንነጋገር ከተባለ ሁላችንም በተቃዋሚነት ቆመን ይህን ዘረኛና አሸባሪ አንባገንነን እንጥላለን ስንል የኑሮ ነገር ስላጋደለብን ሙሉ ጊዜንና ሕይወትን ለትግሉ የሚሰጥ ስለጠፋ ነው ድል እየራቀን፤ በወገን ላይ የሚደርሰው ግፍና በደል እየበዛብን የቀጠለው። እናም እነዚህን መሰሎች ለማውጣት ያሉንን መንከባከብ ሲገባ፤ ስድብና ዘለፋ ከጠላት የሚወረወረው ይበቃል።

No comments:

Post a Comment