"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Monday 18 March 2013

ሃገሬ ............የገብረክርስቶስ ደስታ ግጥም።



አገሬ ውበት ነው...........
ለምለምና ነፋስ የሚጫወትበት
ጸሃይ የሞላበት፣ ቀለም የሞላበት።
አገሬ ቆላ ነው፣ ደጋ ወይና ደጋ
እዚያ ብርሃን አለ ሌሊቱ ሲነጋ።
አገሬ ተራራ ሸለቆ ረባዳ
አገሬ ጅረት ነው ገደልና ሜዳ።
ውሸት ነው በበጋ ጸሃይ አትፋጅም
ክረምቱም አይበርድም፣
አይበርድም፣ አይበርድም።
አገሬ ጫካ ነው
እንሰሳት አራዊት የሚፈነጩበት
በወጥመድ ሳይገቡ ሳይነካቸው ጠላት።
እዚያ አለ ነጻነት።
በሃገር መመካት፣
በተወላጅነት፣
በባለቤትነት፣
እዚያ አለ ነጻነት።
አገሬ ሃብት ነው።
ጎመኑ ስብ ጮማ፣ ቆሎ ክትፎ ስጋ
ድርቆሹ ፍትፍት ነው፣ ቃሪያው ሙክት ሠንጋ።

ጠጁ ነው ወለላ
ከኮኛክ ይነጥቃል የመንደሩ ጠላ።
እህሉ ጣዕም አለው እንጀራው ያጠግባል
በዓሉ ይደምቃል፣
ሙዚቃው ያረካል፣
ጭፈራው ዘፈኑ ችግርን ያስረሳል።
እዚያ ዘመድ አለ።
ሁሉም የናት ልጅ ነው፣
ሁሉም ያባት ልጅ ነው፣
ጠላትም አንዳንዴ ይመጣል መቃብር
ባለጋራም ቸር ነው “ያገር ልጅ ሲቸገር” ።
ገነት ነው አገሬ።
ምነው ምን ሲደረግ !
ምነው ! ለምን ! እንዴት !
ዘራፊ ቀማኛ ምቀኛ ወንበዴ
ጥርኝ አፈር በጁ ስንዝር ወሰን አልፎ
የተቀደሰውን ያፍሪቃ ላይ ደሴት
ባያገኝ ለማርከስ ጠላት ይመኝ እንዴት።
እምቢኝ አሻፈረኝ !
አሻፈረኝ እምቢ !
መቅደስ ነው አገሬ፣
አድባር ነው አገሬ።
እናትና አባት ድኸው ያደጉበት
ካያት ከቅደመ አያት የተረካከቡት
አፈር የፈጩበት፣
ጥርስ የነቀሉበት።
አገሬ ዓርማ ነው የነጻነት ዋንጫ
በቀይ የተጌጠ ባረንጓዴ ብጫ።
እሾህ ነው አገሬ፣
በጀግናው ልጅ አጥንት የተከሰከሰ
ጠላት ያሳፈረ አጥቂን የመለሰ።
አገሬ ታቦት ነው መቅደስ የሃይማኖት
ዘመን የፈተነው በጠበል በጸሎት።
ለምለም ነው አገሬ፣
ውበት ነው አገሬ፣
ገነት ነው አገሬ።
ብሞት እሄዳለሁ ከመሬት ብገባ
እዚያ ነው አፈሩ የማማ ያባባ።
ስሳብ እሔዳለሁ ቢሰበርም እግሬ
አለብኝ ቀጠሮ ከትውልድ አገሬ።
አለብኝ ቀጠሮ
ከትውልድ አገሬ ካሳደገኝ ጓሮ።

ገብረክርስቶስ ደስታ።

No comments:

Post a Comment