"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Thursday 19 April 2012


ታሪክን የኋሊት ‹‹ለትግራይ ተወላጆች የቀረበ ጥሪ››


(አንድ አድርገን ሚያዚያ 11 ፤ 2004 ዓ.ም) ፡-  ቀኑ ህዳር 6 1985 ዓ.ም ነበር ፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ሰሜን አቅጣጫ በምትገኝው በመንበረ መንግስት ቁስቋም ቤተክርስትያን ብዙ ህዝበ ክርስትያን ተሰብስቧል ፡፡ ምክንያቱ በዓለ ቁስቋምንና የጾመ ጽጌን ፍቺ በዓል ለማክበር ነበረ ፡፡ የዕለቱም አስተማሪ አለቃ አያሌው ታምሩ ነበሩ፡፡ አለቃ ‹‹በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን›› ብለው ጀመሩ፡፡ በትምህርታቸውም ስለ እመቤታችን ስደት ፤ ስለ ቁስቋም ታሪክ ፤ ወደ እየሩሳሌም ስለ መመለሷ ፤ ከእመቤታችን 300 ዓመት በኋላ በግብጽ ስለተሰራው የመታሰቢያ ቤተክርስትያን ፤ በዚህ በዓል ምክንያት ኢትዮጵያውያን ነገስታትና ንግስታት ስላደረጓቸው መንፈሳዊ ተሳትፎዎች ፤ ስመ ጥሩዋ ኢትዮጵያዊት ንግስት እቴጌ ምትዋብ በጎንደር ስላሰሯት የደብረ ቁስቋም ቤተክርስትያን  ፤ ስለ ጾመ ጽጌ ፤ ስለ ማህሌተ ጽጌ በዝርዝር አስተማሩ፡፡ ከዚያም በመቀጠል ፤ በእመቤታችን በቅድስት ማርያምና በልጇ ስደት በረከትን ካገኙ የኢትዮጵያ አውራጃዎች አንዱ የሆነው ምድረ ትግራይ ከሌሎች ቅዱሳን የኢትዮጵያ መካናት ጋር የተጣመረ የታሪክ ተዛምዶ ያለው ከመሆኑ ባሻገር ከታቦተ ጽዮን ጀምሮ ለኢትዮጵያ ለተሰጡ ልዩ ልዩ ስጋዊ እና መንፈሳዊ በረከቶች ምንጭና ቦይ ሆኖ የኖረ ነው ፡፡ ዋልድባ ገዳምም ይህን መንፈሳዊ በረከት ከሚገኝባቸው ቦታዎች አንዱ ነው ፤  በአሁኑ ወቅት ህዝቡ የተሰጠውን  ስጋዊ ስልጣን አገሪቱንና ቤተክርስትያንን ከውድቀት ለማንሳት ሊሰራበት ይገባል፡፡ ይህ ሳይሆን ቀርቶ ህዝብና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ስራ ቢሰራ ግን ትዝብትና የታሪክ ተወቃሽነትን ያተርፋል ፤ ያለው ሰፊት ትምህርት ሰጥተዋል ፡፡(የአለቃ አያሌው ታምሩ የመንፈቅ መታሰቢያ ገጽ 26)



የአባታችን አለቃ አያሌው ታምሩ ይህን ለምን እንዳሉ ግልጽ ነው ፤ ዘመነ ደርግ የሰራዊት ብዛት መከታ ሳይሆነው ከትግራይ የተነሱት የሽምቅ ተዋጊዎች ዘንድ ስልጣል በእጃቸው ገብቷል ፤ ዘመነ ደርግ ቤተክርስትያን ከዩዲት ጉዲት እና ከግራኝ መሀመድ በኋላ በአገዛዙ ከፍተኛ ፈተና ላይ የወደቀችበት ጊዜ ነበር ፤ ‹‹ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች።›› መዝሙረ ዳዊት 68፤31  ብሎ መዝሙረኛው ዳዊት እንዳልጻፈ እግዚአብሔር የለም የተባለበት ጊዜም ነበር ፤ ኢትዮጵያ ሐገረ እግዚአብሔር እና እመቤታችን የአስራት ሀገር ብሎ በአውደ ምህረት መስበክ ለአገልጋዮች አስቸጋሪ ወቅት ነበር ፡፡ የእምነት ነጻነት ሀውልት ባይሰራለትም  ለ17 ዓመት የተቀበረበት ጊዜ ነበር ፤ ሀገሪቱም በጊዜው የተረጋጋች አይደለችም ፤  አለቃ አያሌው ማስተላለፍ የፈለጉት መልዕክት ‹‹የያዛችሁትን  ስልጣን ቤተክርስትያንን ከውድቀት ልታነሱበት ይገባችኋል ፤ ይህ ሳይሆን ቢቀር እና ቤተክርስትያንን ከድጡ ወደ ማጡ የምትወስዷት ከሆነ ፤ ለችግሯ የመፍትሄ አካል ባትሆኑ እንኳን የሚነደው እሳት ላይ ማገዶ የምትማግዱባት ከሆነ ፤ እግዚአብሔርንም የሚያሳዝን ስራ ከሰራችሁ ከታሪክ ተወቃሽነት አትተርፉም››  ነው ያሉት፤
በታሪክ አጋጣሚ ሰዎች ስጋዊ ስልጣን ሊኖራቸው ይችላል ፤  ስልጣናችሁን ለሀገር ፤ ለህዝብና ለቤተክርስትያን መልካም በመስራት ካሳለፋችሁ ጊዜያችሁን እንደ ንጉስ ሰለሞን ዘመናችሁ በረከት ይኖረዋል ፤ ንጉስ ሰለሞን ከአባቱ ዳዊት ንግስና ሲቀበል መጀመሪያ እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ ለመነ

‹‹ አቤቱ አምላኬ ሆይ፥ እኔን ባሪያህን በአባቴ በዳዊት ፋንታ አንግሠኸኛል እኔም መውጫንና መግቢያን የማላውቅ ታናሽ ብላቴና ነኝ። ባሪያህም ያለው አንተ በመረጥኸው ሕዝብህ ስለ ብዛቱም ይቆጠርና ይመጠን ዘንድ በማይቻል በታላቅ ሕዝብ መካከል ነው። ስለዚህም በሕዝብህ ላይ መፍረድ ይችል ዘንድ፥ መልካሙንና ክፉውንም ይለይ ዘንድ ፤ ለባሪያህ አስተዋይ ልቡና ስጠው አለዚያማ በዚህ በታላቅ ሕዝብህ ላይ ይፈድ ዘንድ ማን ይችላል?›› መጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ 3 ፤9
‹‹እግዚአብሔርም አለው፦ ፍርድን ትለይ ዘንድ ለራስህ ማስተዋልን ለመንህ እንጂ ለራስህ ብዙ ዘመናትን ባለጠግነትንም የጠላቶችህንም ነፍስ ሳትለምን ይህን ነገር ለምነሃልና እነሆ፥እኔ እንደ ቃል አድርጌልሃለሁ እነሆ፥ ማንም የሚመስልህ ከአንተ በፊት እንደሌለ ከአንተም በኋላ እንዳይነሣ አድርጌ ጥበበኛና አስተዋይ ልቡና ሰጥቼሃለሁ።››  መጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ 3 ፤11-12 አለው ፤
መንፈሳዊነትን የተላበሳችሁ ብትሆኑ እንደ ሰለሞን ማስተዋልንና ጥበብን ከእግዚአብሔር መጠየቅ መልካም ነበር ፤ ነገር ግን መንፈሳዊነቱም ባይኖር የሚሰሩን ስራ ማስተዋል ይገባል ፤ ስልጣን በራሳችን ፍላጎትና ጥረት ብቻ የምናመጣው ነገር አይደለም ፤ የእግዚአብሔርም መልካም ፍቃድ መሆኑን ማወቅ መቻል አለብን  ‹‹ ሥልጣን ከሰማያት እንደ ሆነ ካወቅህ በኋላ መንግሥትህ ይቆይልሃል።›› ትንቢተ ዳንኤል  4፥26 ስጋዊ ስልጣንም ቢሆን ከላይ እንደሚሰጥ ማወቅ መቻል አለብን ፤

በትግራይ ክልል ውስጥ በርካታ የተቀደሱ ቦታዎች ይገኛሉ ፤ ለምሳሌ ያህል ለተዋህዶ እምነታችን ትልቁን ቦታ  የሚይዙትን  የሙሴ ጽላት መገኛ አክሱም ጽዮንና ዋልድባ ገዳምን መጥቀስ ብቻ በቂ ነው ፤ በየዘመኑ የተነሱ ቅዱሳን አባቶቻችን በርካታ አሻራዎቻቸውን በትግራይ ክልል ላይ ጥለውልን አልፈዋል ፤ ይህ ማለት ግን ክልሉ ነው እንጂ ትግራይ መንፈሳዊ ቦታዎቹ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን አምልኮተ እግዚዘብሔር የምትፈጽምባቸው ቦታዎች ናቸው  ፡፡ በጣና ሀይቅ ዙሪያ የሚገኙ ገዳማት የባህር ዳርና የአካባቢው ክርስትያኖች ብቻ አይደሉም ፤ በመላው ሀገሪቱ የምንገኝ የእምነቱ ተከታዮች ጭምርም ናቸው ፤

ከጥቂት አመታት በፊት ለህዳር ጽዮን ዓመታዊ  ክብረ በአል ለማክበር ከእመቤታችን በረከትም ለማግኝት አክሱም በሔድኩበት ጊዜ የአካባቢው ማህበረሰብ በጣም ደስ አሰኝቶኛል ፤ ከንግስ መልስ ቤታቸው ያዘጋጁትን እንድንቀምስላቸው ምዕመኑን በሽሚያ ነበር ወደ ቤታቸው የሚወስዱት ፤ ሰው በልቶ  የሚጠግብ እስከማይመስላቸው ድረስ ከአንድ ክርስትያን የሚጠበቀውን ነገር አድርገውልናል ፤ ጽዮን ለእነርሱ ብዙ ነገራቸው ናት ፤ የክርስትና መነሻ የሆነውን አክሱምንም በተለየ አይን ነው የሚመለከቱት ፤ ለእምነታቸው ያላቸው ተቆርቋሪነትም መልካም ነው ፤ ለበርካታ ጊዜያት አክሱም ላይ መስኪድ ለመስራት ሙስሊም ማህበረሰብ ጥያቄ አቅርበው ነበር ፤ ነገር ግን  እስከ አሁን አንዱም ተቀባይነት አላገኝም ፤ በጣም የሚገርመው ነገር አክሱም ላይ አይደለም መስኪድ ሊሰራ ቀርቶ ሙስሊም ቢሞት እንኳን ከአክሱም ውጪ ነው የሚቀበረው ፤ ታዲያ ይህ ማህበረሰብ የዋልድባ የስኳር ልማት ደግፎት ነው ወይስ ተቃውሞ ነው የተቀመጠው ? የሚል ጥያቄ ተጫረብኝ

ትግራይ ክልል  የሚገኙ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ክርስትያኖች ለምን በዋልድባ ገዳም ላይ የሚሰራውን የስኳር ልማት እንዳልተቃወሙ አንድ የክልሉን ተወላጅ የቅርብ ጓደኛዬን ጠይቄው እንደተረዳሁት  ‹‹በክልሉ አብዛኛው ህዝብ የኢህአዴግ ደጋፊ ነው ፤ ሰው የፈለገውን የፖለቲካ ፓርቲ መደገፍ ህገመንግስታዊ መብቱ ነው ፤ ማህበረሰቡ ኢህአዴግ የሚሰራውን የስኳር ልማትን በውስጡ ቢቃወምም በአደባባይ ግን ተቃውሞውን መግለጽ አይፈልግም ፤ ይህን ልማት ስለ እምነቱ ብሎ መቃወም ማለት በአካባቢው ነዋሪዎች እና የመንግስት ሹሞች ‹‹ተቃዋሚ›› የሚል ስም ያሰጠዋል ፤ ይህን ደግሞ የእምነቱ ተከታዮች ተወልደው ባደጉበት ፤ በኖሩበት እና ለቁም ነገር በበቁበት  ቀዬ ስሙን አይፈልጉትም ፤ ይህን ቢቃወም ነገ የሚደርስበት መከራ ጫንቃው ሊሸከመው የማይችለው ነው ፤ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚደርስበት መከራ ይከብዳል ፤ እምነቱ ላይ የማይገባ ነገር ሲያደርጉ ቢመለከቱም ውስጥ ውስጡን ጥያቄ በማቅረብ እንዲስተካክሉ አስተያየቱን ይሰጣል እንጂ በይፋ መቃወም ማለት የማይታሰብ ነው፡፡›› ብሎኛል ፡፡

ማንም ሰው የፈለገውን የፖለቲካ ፓርቲ መደገፍ መብቱ ነው ፤ ይህን ጽሁፍም የምታነቡ በርካቶች የኢህአዴግ አባል  ወይም ደጋፊ ልትሆኑ ትችላላችሁ ፤ በዚህ ላይ ምንም አይነት ተቃውሞ የለንም ፤ ነገር ግን የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታይ የሆነ የኢህአዴግ አባልም ይሁን ደጋፊ በቤተክርስትያን ላይ የተጋረጠውን አደጋ ፤ የወደፊት ፍራቻውንና ስጋቱን በመግለፅ  በጉዳዩ ላይ  ተቃውሞውን ማሰማት መቻል አለበት ብለን እናስባለን ፡፡ አባል ብትሆኑም በዚህ ነገር ላይ አቋም ይኑራችሁ ፤ ጉዳዩን ሳትገነዘቡ አትደግፉ ፤ ሳታውቁትም መንግስት ስላቀረበው ብቻ አስተያየታችሁን አትስጡ ፤ እውነታውን እወቁ የራሳችሁ አቋምም ይኑራችሁ ፤ የፓርቲው ደጋፊ ስለሆናችሁ ብቻ መንግስት ያቀረበውን ነገር አትደግፉ ፤ ተቃዋሚ ስለሆናችሁም ብቻ አትቃወሙ ፤ ‹‹ትውልድ ይሄዳል፥ ትውልድም ይመጣል ።›› መጽሐፈ መክብብ 1፤3  ዛሬ አደጋውን ሳትረዱት ደግፋችሁ ነገ ገዳሙ ላይ ችግሩ አይኑን አፍጦ ሲመጣ ከህሊናችሁ በላይ ወቃሽ አታገኙም ፤ ሁሉም እንዳለ አይቆይም እኛ እናልፋለን ፤ ተተኪዎቻችን ደግሞ ይመጣሉ ፤ መንግስት ለሀገሪቱ እድገት ሲል ለሚያከናውነው ለሀገርና ለህዝብ የሚጠቅም የልማት ፕሮግራሙን እንደግፋለን ፤  ጨለምተኛ አመለካከትም የለንም ፤ እንደዚያው ደግሞ ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚያመዝነውን ፤ የገዳሙን ህልውና የሚፈታተነውን እንቃወማለን

ኢትዮጵያ ብዙ መከራዎችን አሳልፋለች ፤ ብዙዎቹ መከራዎች ከውጭ ወራሪዎች ቢደረሱም ከውስጥ ሀይሎችም ከደረሰው ጥቃት ያልተናነሰ መከራ በቤተክርስትያንና በሀገር  ላይ ብዙ መከራ ደርሷል ፤ ይህች ቤተክርስትያን ከዘመነ አክሱም ጀምሮ አሁን እስካለንበት የኢህአዴግ ዘመን ድረስ ብዙ መንግስታትን አሳልፋለች ፤ ፈሪሀ እግዚአብሔር ያላቸው ነገስታት ለቤተክርስትያን እና ለህዝበ ክርስትያን በርካታ መልካም ተግባሮችን አከናውነው ወደማይቀረው አለም አልፈዋል ፤ ስማቸውም በመልካም እየጠራነው እነርሱንም እየዘከርናቸው እንገኛለን ፤ ሌሎች ደግሞ የምትጠፋ መስሏቸው ጦር መዘውባታል ፤ በዘመናቸው ቤተክርስትያኒቷን ለማፍረስ ድንጋይ  አንስተውባታል ፤ አሳት ለኩሰውባታል ፤ እሷ ግን የመጣውን መከራ ተቋቁማ እጃቸውን ያነሱባትን ወደ ኋላ ትታ አሁን እኛ ትውልድ ላይ ደርሳለች ፤ አሁን ደግሞ ገዳሟ ላይ ሸንኮራ ለመትከል ተነስተውባታል  ፤ እኛ እናልፋለን እነርሱም ያልፋሉ ፤ እነሱ የሚያልፉት ግን ከግራኝ መሀመድ ያልተናነሰ ጥቁር አሻራ ለትውልድ ጥለው ነው ፡፡ ትውልድ ደግሞ ይጠይቃል ፤ ዛሬን ብቻ አንመልከት ነገ ጥያቄ አለ ፤ ያለፉት መንግስታት መጥፎ ሲሰሩ ትውልድ ስማቸውን በመጥፎ እንዳያነሳ በከፍተኛ ጥንቃቄ መረጃ ይደብቃሉ ፤ እውነታዎችን ደብዛቸውን ለማጥፋት ጉድጓድ ይቆፍራሉ  ፤ ዛሬ ግን መረጃው ሁሉ አደባባይ ላይ ስላለ የሚደበቅ ነገር አይኖራቸውም ፤ ስራቸው ትርፉ ገብስ ነው የሚሆንባቸው ፡፡    

ዋልድባ ገዳም በትግራይ እና በአማራ ክልል የሚገኝ ታላቅ ገዳም ነው ፤ ጉዳዩ ይመለከተናል ብለው የብአዴን አባላት ከሳምንት በፊት መወያየታቸው ምዕመኑም ስጋቱን በጥያቄ መልክ ማቅረብ ችሏል ፤ ተገቢ መልስ ባያገኝም ፤ ስብሰባውን የሚመሩት የመንግስት ባለስልጣን ሰው በትምህክት ‹‹ዋልድባ ማለት የትግራይ ህዝብ ነው እናንተ ምን አገባችሁ›› ብለው ተናግረው ነበር ፤ ‹‹ ዋልድባ ገዳም የትግሬ የአማራ የሚባል ገዳም አይደለም ፤ ዋልድባ አለማቀፋዊ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስያን ገዳም ነው›› ተብሎ መልስ ተሰጧቸዋልት ፤  ቤተክርስትያናችን ጎጠኝነትንና ጠባብ አስተሳሰብን ለልጆቿ አትሰብክልንም ፤ ማለት የፈለጋችሁት ገብቶናል ፡፡ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ራሳቸው ከብሄር እና ከጎጠኝነትና ከጠባብ አመለካከት መውጣት አለመቻላቸውን የሚያስረዳ አስተያየት ነበር  ፤ የያዛችሁት ጎጥ ለናንተም አይጠቅምም ፤ ለምን ይህ አመለካከት ኖራችሁ አንልም ፤ ነገር ግን ከዚህ አስተሳሰብ ትወጡ ዘንድ ጸሎታችን ነው ፤
ቤተክርስትያን የተመሰረተችው በጌታችን በመድሀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ደም አማካኝነት ነው፡፡ በማንም ላይ የተደገፈች አይደለችም ፤ ምርኩዟ ክርስቶስ በመሆኑ እስከ አሁን ቆይታለች ፤ በትግራይ ክልል የሚገኝው ዋልድባ ገዳም ደግሞ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚፈጸምበት ቅዱስ ቦታ ነው ፤ ዓለም በቃን ያሉ የላመ እና የጣፈጠ ነገር ትነው ገዳም የገቡ መነኮሳት ቀን ከሌት ስለ ቤተክርስትያን ስለ ሀገር ፤ ስለ ህዝብ ሰላም ፤ የሚጾሙበት የሚጸልዩበት ቦታ ነው ፤ ይህን እውነታ ብታውቁትም ደግመን እንነግረችኋለን፡፡ በአካባው የምትገኙ ምዕመናን እየደረሰባችሁ ያለውን መከራ ከአይን ምስክር ሰምተናል ፤ በይፋ መቃወም የሚያመጣው አደጋም ይገባናል ፤ ነገር ግን በጸሎታችሁ በርቱ እንላለን፡፡ ከወደ ጎንደር ከረር ያለ ተቃውሞ የደረሰው ሀገሩ ጎንደር ስለሆነ ነው ፤

‹‹በአሁኑ ወቅት ህዝቡ የተሰጠውን  ስጋዊ ስልጣን አገሪቱንና ቤተክርስትያንን ከውድቀት ለማንሳት ሊሰራበት ይገባል፡፡ ይህ ሳይሆን ቀርቶ ህዝብና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ስራ ቢሰራ ግን ትዝብትና የታሪክ ተወቃሽነትን ያተርፋል›› አለቃ አያሌው ታምሩ



 ቸር ወረ ያሰማን

No comments:

Post a Comment