"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Thursday 6 September 2012

ሐዘን የሸሸገው ፈገግታ


ሐዘን አጥንት ሲደርስ ደግ አይደለም:: ሰውም እግዜሩም አይወዱትም:: ለአገርም አይጠቅምም ለጠላትም ደስ አይበለው:: እንዲህ አገር ነቅሎ ሙሾውን ሲያስነካው ተዉ እሚል ይጥፋ? ያ ምስኪን ትዝ አለኝ... ጃንሜዳ ጋር ሞቶ እሚቀብረው ሲያጣ አዝኖ ወደቤቱ የተመለሰው ሃሃሃሃ…:: ለማንኛውም ሕገ መንግስቱ እንደሚለው የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲያርፍ ወይም በሞት ሲለይ አንድ ቀን ብሔራዊ ሃዘን ይታወጃል:: እንደ በረከት ስምኦን ቢሮ አሥራ አራት ቀን መሆኑ ነው:: [በየቀኑ የሚጣስን ሕገመንግስት አንስቶ መከራከሩ ፅንፈኛ ያስብለኛል ስለዚህ ይለፈኝ] በዛ ላይ ዋሽንት አለ [ለአንዳንዶች vuvusela ሆኖባቸዋል]:: ስለዚህም እንደ አንድ ሐዘናችንን ለማስረሳት እንደሚጥር ልማታዊ አፅናኝ በለቅሶው አካባቢ ከተሰሙት ንግግሮች ጀምሮ ወሬው እንዳመራን ውል አልባ ጨዋታ ብንጨዋወትስ...

ሰሞኑን እንደ ጆሮ ስቃዩን ያየ (ሰደቃውን የበላ) የለም... ጆሮ ሆይ አድናቂህ ነኝ!

የልማታዊው በረንዳ አዳሪ አስተያየት፣ "አባታችንን ተማምነን ነው በረንዳ የምናድረው" የሚለው አስገራሚ ለቅሶ የልማታዊውን እስረኛ ሰሜ ባላገሩን ቃለ ምልልስ ያስታውሰናል፤ "በመታሰሬ በጣም ደስተኛ ነኝ መንግስቴንም አመሰግነዋለው" ነበር ያለው ሰሜ ከእስር ቤት እንደወጣ [ሰሜ ሮሚዎን ሆኖ ትያትር እንደተጫወተ ላስታውስ]፡፡ ሰሜን ተንጠላጥለን ወደ ሁዋላ ስንሄድ "ታንክ ተደግፎ መጽሐፍ ያነብ ነበር" ያለው የኢትዮፈርስት ዌብሳይት  አዘጋጅ ቤን፣ "HR 2003ን ከማፅደቃቸው በፊት የአሜሪካን ሴናተሮች ጉዳዩን መላልሰው እንዲያዩት የመከሩት የብቸና ገበሬዎች፣ የአሜሪካንን ኢምፔርያሊዝም ከተሳሳተ ርዕዮተ-ዓለሙ እንዲታረም ያስጠነቀቁት የቦረና አርብቶ አደሮች"
...

ለቅሶው የኪራይ ሰብሳቢዎች መጠቀሚያ እንዳይሆን የመከሩምትን ጨምሮ "እንግዲህ ዓለም ምን ይዋጣት!" ብለው ስለ አለማችን ያለቀሱም ነበሩ:: ዲሞክራሲውን በተደላደለ መሰረት ላይ ማስቀመጣቸው፣ እንደ ክርስቶስ ስለሰው ልጆች መሰዋታቸውን፣ ለዚህ ምስኪን ሕዝብ ሲሉ ፀጉራቸውን ተበጥረው፣ ቀበቶአቸውንም አስረው እንደማያውቁ ነግረው ክፉኛ አስደንግጠውናል:: ስለ ዴሞክራሲና ፍትህ፣ እኩልነት፣... ምስክሮች ሰምተናል:: ነዋይም "የሙሴን በትር የተቀበለ" ሲል አቀነቀነ:: የዋልድባ ገዳም አባቶችም "እናንተ ናችሁ መተተኞች" ተብለው መከራ አዩ ሲባል "ኢትዮጵያ ቀኑ ጨለመባት" የሚልም መዝሙር ሰማን... ወይ ጆሮ:: ለአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያምም ከዋልድባ፣ አወልያና አበበ ገላው እንዲጠነቀቅ ምክር የለገሱ ብቅ አሉ:: የአባይ ግድብ በስማቸው እንዲሆን ወይንም አዲስ የብር ኖት በእርሳቸው ምስል እንዲታተም፣ ሐሳብ ያቀረቡና ጉዳዩን ሕዝባዊ ለማድረግ የሚሰሩም ታይተዋል:: የለቅሶ አይዶል ሊዘጋጅ እንደሚችልም ጭምጭምታ አለ::

አብዮታዊ ስያሜ ያላቸው ንግድ ቤቶችም ቁጥራቸው ጨምሯል፡፡

እነ "ጀግና አይሞትም ስጋ ቤት"፣ እነ "የስፎርሜሽን ዕቅዱ ይሳካል ሻይ ቤት"፣ እነ "ውሃ ማቆር ባርቤሪ"፣ እነ "አባይ ይገደባል ምግብ ቤት"፣ እነ "ቢፒ አር ልብስ ስፌት"፣ እነ "ባድሜ የኛ ናት የአልጀርሱ ስምምነት ውሳኔ ግን ተገቢ አይደለም ባልትና"፣ እነ "ሬነሳንስ ልማታዊ ቡና ቤት"ን ለሐዘን ከሚሆን ጥሬና ጥብስ እና ከተከዘ አስተናጋጅ ጋር ተቀላቅሏል:: "ጣት እንቆርጣለንና በሊማሊሞ አቋርጡ ችርቻሮ መደብር" ሃሃሃሃ….

ስለ ደርግ ብዙ አላውቅም:: ትዝ እሚለኝ "ሾላ እርግፍ እርግፍ" የሚባለው ጨዋታ ብቻ ነው:: እንግዲህ ዳርዳርታው ምነው አነሰ የሚል ክስ ከመጣ በሚል መሆኑ ነው:: ጎልማሶች እንደሚያወሩት ከሆነ ደርግን የሚስተካከል ያፈጠጡ፣ ዉሃ የማያነሱና የጽሑፎቹ ቀለም ሳይደርቅ ዋጋ ቢስ የሚሆኑት መፈክሮችን ያህል ውሸት የባህሪው የሆነው ኢሕአዴግ እንኳን መፈብረክ አልቻለም::

"ያለምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም" ተብሎ በ"አብዮት ልጆችዋን በላች" ሲደመደም፣ እንዲህም ተብሎ ሲገጠም
"የሞተው ወንድምሽ
የገደለው ባልሽ
ሃዘንሽ ቅጥ አጣ
ከቤትሽም አልወጣ"

ፖለቲካው ሴሰኛ ሲሆን "ባብዮት ግዜ የለም ትካዜ" እየተባለ ሲራገብ፤ በመጨረሻም በስሪያ ላይ ተጣበቀው ሰፈሩን የሚያሽኮረምሙትን ውሾች ቀጥቅጦ የሚያላቅ ወንድ ጠፍቶ፣ ሁሉም ቤቱ መሽጎ!

በመሃል "ተፈጥሮን በቁጥጥር ስር እናውላለን" የሚሉ መፈክሮች እስኪሰለቹ ሲለፈፉ… ወይ ተፈጥሮ!!! ምን መስሎን ይሆን?!

ይህንን ያህል ከተጫወትን ይበቃናል:: ሐዘን ላይ ነሽና/ነህና ቀልደህ ሞተሃል ብንባል እንቀበላለን!

No comments:

Post a Comment