"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Monday 15 October 2012

ሶስት ኢጲስ ቆጶሳት ለፓትርያሪክ እጩነት ቀረቡ፤ የኢት.ኦ.ተ.ቤ.ክ እርቀ ሰላም ሊወርድ ይችል ይሆናል ተብሎ ይገመታል!





መንግስት አቡነ ጳውሎስን ለመተካት 3 ጳጳሳትን አጨ (በሁለቱ ሲኖዶሶች እርቅ ዙሪያ አዳዲስ መረጃዎች ዘ-ሐበሻ እጅ ገቡ)- መንግስት አቡነ ጳውሎስን ለመተካት ያዘጋጃቸው 3ጳጳሳትን የዘ-ሐበሻ ምንጮች ደረሱበት - ”መንበሩን ኢትዮጵያ ገብቶ የመረከብና ያለመረከብ
ምርጫ የፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስ ነው” - የአቡነ ጳውሎስን “ሌጋሲ” የሚያስፈጽሙት አቡነ ገሪማ ይገኙበታል (ዘ-ሐበሻ) በአዲስ አበባ የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ እና በውጭ ሃገር የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ ሊቀመጡ መሆኑ ተሰማ። የዘ-ሐበሻ ታማኝ ምንጮች እንደጠቆሙት ከሆነ በአዲስ አበባ የሚገኘው ሲኖዶስ ከጥቅምት 21 ቀን 2005 ጀምሮ እንዲሁም በውጭ ሃገር የሚገኘው ሲኖዶስ ደግሞ ጥቅምት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ጉባኤያቸውን ይጀምራሉ።
በአዲስ አበባም ሆነ በውጭ ሃገር የሚገኙት ሁለቱ ሲኖዶሶች በዚህ ጉባዔያቸው ላይ “በአቡነ ጳውሎስ ቦታ ላይ ማን ይሾም? 4ኛው ጳጳስ አቡነ መርቆርዮስ ወደ መንበራቸው ይመለሱ ወይስ አይመለሱ? መንግስት የራሱን ጉዳይ እንዲያስፈጽሙ ያስቀመጣቸው 3 ጳጳሳት መካከል አንዱን እንምረጥ ወይም አንምረጥ?” በሚሉት ዋነኛ ጉዳዮች ላይ እንደሚወያዩ የዘ-ሐበሻ ምንጮች ጠቁመው ከዚህ በተጨማሪም ይህ በሁለት ሃገራት፤ በሁለት ሲኖዶሶች የሚደረገው ጉባኤ ሌሎች የቤተክርስቲያን ጉዳዮችን ያነሳል ተብሎ ይጠበቃል።

ፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስ
አቡነ ጳውሎስ ካረፉ በኋላ በአቃቤ መንበርነት የተሾሙት አቡነ ናትናኤል ለአራተኛው ጳጳስ አቡነ መርቆርዮስ “ይድረስ ለብጹእ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስ ርዕሳነ ሊቃነ ጳጳሳት ዘ-ኢትዮጵያ” በሚል ደብዳቤ መላካቸውን እንደበጎ ጎን የተመለከቱ የሃይማኖት አባቶች የአቡነ መርቆርዮስን ህጋዊ ፓትርያርክነት ደብቤያቸው መስክሯል ብለዋል። አቃቤ መንበር አቡነ ናትናኤል በስደት የሚገኘው ሲኖዶስ ወደ ሃገር ቤት እንዲገባ በደብድቤ ከመጠየቃቸውም በላይ ፓትርያርኩ በሕይወት እያሉ ሌላ መሾም የለበትም ከሚሉት ወገኖች ቆመዋል የሚሉት ምንጮቻችን በተለይ ከሥርዓቱ ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያላቸውና የኢሕአዴግን ጉዳይ ለማስፈጸም የሚፈልጉ አንዳንድ ጳጳሳት አዲስ ፓትርያርክ እንዲሰየም በመወትወት ላይ ናቸው።
መንግስት በፓትርያርክነት እንዲሾሙ የሚፈልጋቸው 3 ጳጳስት እነማን ናቸው?
የዘ-ሐበሻ ታማኝ ምንጮች እንደሚሉት መንግስት በተለይም በሕወሓቱ አባይ ጸሃዬ የሚመራው ቡድን 3 ጳጳሳትን

እንዲሾሙ አጭቶ አቅርቧል። የነዚህ አባቶች ዝርዝርም ለዘ-ሐበሻ ምስጢሩ ከአዲስ አበባ ሾልኮ ገብቷል።
1ኛ እጩ፦ አቡነ ማቲያስ


አቡነ ማቲያስ
የመጡት፡ ከትግራይ መንግስት በፓትርያርክነት እንዲቀምጡ ከሚፈልጋቸው አባቶች መካከል አንዱ አቡነ ማቲያስ ናቸው። አቡነ ማቲያስ ዛሬ ቤተክርስቲያን ለ3 እንድትከፈል ምክንያት ከሆኑት መካከክ አንዱ ናቸው እየተባሉ ይተቻሉ። በተለይም ሃገር ቤት ካለው
ሲኖዶስ፣ ውጭ ካለው ሲኖዶስ ውጭ የሆነ ገለልተኛ ቤተክርስቲያን በውጭ ሃገር በማቋቋም የመጀመሪያው ናቸው። በአቡነ ተክለሃይማኖት የፕትርክና ዘመን ተወግዘው የነበሩት እኚሁ አባት “አቡነ ማቲያስ” የሚለውን ስማቸውን ሁሉ ተነጥቀው ነበር። በዚህም ወቅት ገለልተኛ ቤተክስቲያን አቋቁመው ቤተክርሲያንን ለመከፋፈል ሞክረዋል ተብለው ይተቻሉ። እንደ ዘ-ሐበሻ ታማኝ ምንጮች ዘገባ ከሆነ አቡነ ማቲያስ በቤተክርስቲያን ተወግዘው ከነበሩባቸው ምክንያቶች መካከል በወቅቱ መንበራቸውን ጥለው በመውጣት የኢዲዩ አባል ከመሆናቸውም በላይ ሌሎች ምክንያቶችም ይጠቀሳሉ።
በአሁኑ ወቅት በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ሆነው በማገልገል ላይ ያገለገሉት አቡነ ማቲያስ በሕወሓት ሰዎች ለቤተክርስቲያን ፓትርያርክነት እንዲመረጡ ከታጩት መካከል አንደኛው ናቸው።
2ኛ እጩ፦ አቡነ ጎርጎርዮስ የመጡት ከትግራይ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳዊ የምስራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሲሆኑ በመንግስት ለፓትርያርክነት የታጩት ለአቡነ ጳውሎስ ከአቡነ ገሪማ ቀጥሎ የሚቀርቡ ሰው በመሆናቸውና እርሳቸው የሚከተሏቸውን ሁሉ ስለሚያስፈጽሙ፤ ለስርዓቱም ታማኝ በመሆናቸው ነው ሲሉ የዘ-ሐበሻ ምንጮች ተናግረዋል።

3ኛ እጩ፦ አቡነ ገሪማ
የመጡት፡ ሸዋ ከሟቹ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ያልተናነስ የማዕረግ ስም ያላቸው “ብጹዕ ዶ/ር አቡነ ገሪማ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ዋና ጸሃፊ፣ የቤተክርስቲያን የውጭ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ፣ የድሬደዋ ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ” 3ኛውና ዋነኛው እጩ ናቸው። ጠ/ሚ/ር ሃይለማርያም ደሳለኝ የአቶ መለስን ሌጋሲ አስፈጽማለሁ እንጂ የሚለወጥ ነገር የለም እንዳሉት ሁሉ አቡነ ገሪማም የአቡነ ጳውሎስን “ሌጋሲ” ሊያስፈጽሙ ነው የሚመረጡት እየተባባሉ የሃይማኖት አባቶች ያወሩባቸዋል። በተለይ መንግስት ቤተክርስቲያን ፓትርያክ ከሸዋ ፓትርያርክ መመረጥ አለበት የሚሉትን (ወ እጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ተብሎ ፓትርያርኩ ስለሚጠራና የአቡነ ተክለሃይማኖት መንበር ላይ ስለሚቀመጥ ከሸዋ ነው መመረጥ ያለበት ለሚሉ በተለይ የገለልተኛ ቤ/ክ ድጋፍን ለማግኘት) አቡነ ገሪማን ማስቀመጥ ይፈልጋል።
ሆኖም ግን በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ያለው ሲኖዶስ በአብዛኛው በሕወይወት ያሉት ፓትርያርክ መንበሩን እንዲቀመጡበት ይፈልጋል። ከጥቂት የስርዓቱ ደጋፊዎች በስተቀርና ከወሎ ፓትርያርክ ተመርጦ አያውቅምና ከወሎ ይመረጥ የሚሉ ሊቃነ ጳጳሳት በቀር ቤተክርስቲያን አንድ እንድትሆንና በስደት ያለው ሲኖዶስ እንዲገባ ይፈልጋሉ። በተለይ እንደ አቡነ ገብርኤል ያሉ አባቶች የቤተክርስቲያን አንድ መሆን ሳይሆን ከወሎ ፓትርያርክ መመረጥ እንደሚያሳስባቸው የዘ-ሐበሻ ምንጮች ጨምረው ገልጸዋል።
በአዲስ አበባ ያለው ሲኖዶስ ከጥቅምት 12 ቀን 2012 ጀምሮ በሚያደርገው ጉባኤ በተለይ ከስደተኛው ሲኖዶስ ጋር የተጀመረው እርቅ ዙሪያ አንድ ውሳኔ ላይ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላ በኩልም ከጥቅምት 21 ቀን 2012 ዓ/ም ጀምሮ በኦሃዮ ደብረ መድሃኒት መድሃኔዓለም ቤ/ክ በሚደረገው ጉባኤ ላይም ተመሳሳይ ውሳኔዎች ይጠበቃሉ። ውጭ ካለው ሲኖዶስ በኩል የአቡነ ጳውሎስ መንበር ወትሮም የሚገባው ለኔ ነው በሚል መንበሩን ለመረከብ ዝግጅቱ ሲሆን “ሃገር ቤት የመግባትና ፕትርክናውን የመረከብና ያለመረከብ ምርጫ ግን የፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስ እንደሚሆን” ምንጮቻችን አስረድተዋል። 4ኛው ፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስ ቦታውን የሚይዙ ከሆነ የቤተክርስቲያን አንድነት ይመጣና መከፋፈሉ እንደሚቀር ተስፋ የሚያደርጉት እነዚሁ ምንጮች ኢትዮጵያ ያለው ሲኖዶስ ፓትርያርክ እያለ ዳግም ለ2ኛ ጊዜ ስህተት በመስራት ፓትርያርክ የሚሾም ከሆነ ቤተክርስቲያን እንደተከፈለች ትኖራለች ሲሉ ስጋታቸውን
ይገልጻሉ፡:
በአዲስ አበባ ያለው በተለይም የወያኔን መንግስት የሚደግፉ አባቶች የፓትርያርክ አቡነ መርቆርዮስን መመለስ ከማይፈልጉባቸው ምክንያቶች መካከል አንደኛው፤ የፓትርያርክነታቸው ዘመን የሚቆጠረው ከ1981 ዓ.ም ጀምሮ በመሆኑ የአቡነ ጳውሎስ ሕጋዊ ያልሆነ ፓትርያርክነትን በታሪክ እርቃኑን ስለሚያስቀረውና ለወያኔም ትልቅ ሽንፈት ስለሚሆን ነው። ፓትርያርክ መርቆርዮስ ከ1981 ዓ.ም ጀምሮ በፓትርያርክነት ያገለገሉ ተብሎ የሚገለጽ ከሆነ የአቡነ ጳውሎስ በመሃል ላይ መግባት ምን ተብሎ ሊጠራ ነው?? ሲሉ የሚጠይቁት እነዚሁ ምንጮች ለሲኖዶሶቹ እርቅ እንቅፋት ሊሆን የሚችለውም አንደኛው ጉዳይ ይህ ሊሆን ይችላል ይላሉ፡፡






No comments:

Post a Comment