"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Monday 15 October 2012

የበአሉ ግርማ ጆሮጠቢ “የማውቀውን ሰላይ ካባረርኩማ የማላውቀውን ይተክሉብኛል” (በአሉ ግርማ)






              በኛ ዘመን የብእር ሰው ሆኖ መፈጠር መረገም ሆኖ ይሰማኛል። ከቡቃያው የሚነጋገር፣ በሁዳዱ ላይ ሽምጥ ፈረስ የሚጋልብ፣ ውሎው ከዋልካው፣ ማምሻው ከመልካው የሆነ ገበሬ እንዴት እድለኛ ነው? የኛ ዘመን ብእረኛ ህይወቱ በሰላዮች የተከበበ ነው። ተፈጥሮው ነውና አለመፃፍ አይችልም። መፃፍ ደግሞ አደጋ ነው። በአሉ ግርማ እንዲህ ባለ ችግር ውስጥ አልፎ፣ በከንቱ ያለፈ ደራሲ ነበር። ደርግ ብዙ ሰላዮች መድቦበት ነበር።
በአሉ ግርማ ምንም እንኳ ከደርግ ሰዎች ጋር በቅርብ ይሰራ የነበረ ሰው ቢሆንም ህሊናው ግን ነፃ ነበር። የደርግ የፀጥታው መስሪያ ቤት የበአሉን ነፃ መንፈስ በማወቁ፣ ነፃ ለቆት አያውቅም። በሰላዮቻቸው ከበውት ኖረዋል። በአሉ ግርማን እንዲሰልሉ ከተመደቡት አንዱ አይነስውር ለማኝ ሆኖ ነበር የሚተውነው። በአሉ ግርማ መኪናውን ውቤ በረሃ አቁሞ፣ እዚያው መኪና ውስጥ ሆኖ ሲቀመቅም፣ አይነስውር መሳዩ ለማኝ ወደ በአሉ መኪና ጠጋ ብሎ ይለምናል፣
“ስለ መድሃኒያለም፣ በቀን ጨለመብኝ። ሌትና ቀኑ ተደባለቀብኝ። በኔ የደረሰ በዘርማንዘራችሁ አይድረስባችሁ። ስለመድሃኒያለም ስትሉ እርዱኝ እባካችሁ።”
ይህ ለማኝ ሰላይ መሆኑን ግን በአሉ ግርማ ገና ድሮ አውቆ ነበር። ሆኖም ያላወቀ መስሎ በመጣ ቁጥር አስር ሳንቲም ይሰጠዋል። ሰላዩም አይኖቹን እንደ ፀደይ የቢራቢሮ ክንፍ ብልጭ ድርግም እያደረገ አስር ሳንቲሟን ተቀብሎ፣ በአሉ ግርማ ከማን ጋር እንዳመሸ ተመልክቶ ሲያበቃ፣ በነጋታው በማያዩት አይኖቹ ያየውን ለተስፋዬ ወልደስላሴ ቢሮ ሪፖርት ያደርጋል። ይህ ድብብቆሽም ለረጅም ጊዜ ቀጠለ።
ከእለታት አንድ ቀን በአሉ ግርማ እና ስብሃት ገብረእግዚአብሄር የበአሉ መኪና ውስጥ ቁጭ ብለው እያወጉና እየቀመቀሙ ነበር። ስብሃት እንዳጫወተኝ በመካከሉ የበአሉ ደምበኛ የሆነው አይነስውር ለማኝ መጣ፣
“ስለ ጊዮርጊስ…በቀን የጨለመብኝ…”
አስርሳንቲሙን ከተቀበለ በሁዋላ የሚያየውን አይቶ ተመልሶ ሄደ። በዚህ ጊዜ በአሉ ግርማ ለስብሃት እንዲህ አለው፣
“ለማኝ አይደለም። ሰላይ ነው…”
“እንዴት አወቅህ?”
በአሉ ግርማ እንዴት እንዳወቀ ለስብሃት አጫወተው። በዚህ ጊዜ ስብሃት በጣም ተበሳጨና እንዲህ አለው፣
“እንደነቃህበት ነግረህ ለምን ቆሌውን ገፈህ አታባርረውም? ለምንድነው በየቀኑ አስርሳንቲም የምትገብረው?”
በአሉ እየሳቀ እንዲህ መለሰ፣
“የማውቀውን ሰላይ ካባረርኩማ የማላውቀውን ይተክሉብኛል”





No comments:

Post a Comment