"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Tuesday 19 June 2012

አበበ ባልቻ እንደ ሕወሐት?




ከተስፋዬ ገ/አብ
“ሰው ለሰው” የተባለው ድራማ በድንገት ከመጠናቀቁ ጋር በተያያዘ በርካታ አስተያየቶች እየተሰጡ ነው። ትኩረቴን የሳበው ግን ስለ ተዋንያኑ ውክልና ፌስ ቡክ ላይ የተሰራጨው ወግ ነው። ይችን ቁራጭ መታጥፍ ለመክተብ መነሻ ሆኖኛል።
አበበ ባልቻ ሲተውነው የቆየው ገፀባህርይ (አስናቀ አሸብር) እንደ ህወሃት ወኪል ተሰይሞአል። አስናቀ በጠባዩ ለሃገሪቱ ደንታ የለውም። ገንዘብ በጣም ይወዳል። አብሮአደጉን መስፍን ሊበቀለው ይፈልጋል። ተሳዳቢ ሲሆን፣ በጉልበቱ ይመካል። በቅጥረኞቹ በኩል ሰዎችን ያስደበድባል፣ ያስገድላል። ሃብታም ካገኘ ሊዘርፈው በማሰብ ያንዣብባል። ያም ሆኖ ግን አስናቀ መጨረሻው አላማረም። ንብረት ያከማቸበትን አዳራሽ ሲከፍተው፣ በህገወጥ መንገድ ያከማቸው ንብረት ብን ብሎ ጠፍቶአል። የነበረውን ጥሬ ገንዘብ በሙሉ ወዳልታወቀ ሃብታም፣ (አላሙዲ?) በማዛወሩ በድንገት ባዶውን ቀረ። እና የደም ግፊት? አንቀጥቅጦ ገደለው። የቅርብ ረዳቱ እያሳቀበት ህይወቱ አለፈች።

መስፍን የተባለው ገፀባህርይ በፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ተመስሎአል። ማህሌት ደግሞ የኢትዮጵያ ምሳሌ ነበረች። የመስፍንና የማህሌት ሁለት ልጆች የኢትዮጵያ ህዝብ ወኪሎች ኖረዋል። ሴቷ ልጅ ውጭ ሃገር በስደት ላይ፣ ወንዱ ደግሞ (ብሩክ) በአገር ቤት ይኖራሉ። ውጭ ሃገር ያለችው ሴት ልጅ በዚያው ቀልጣ ቀርታለች። ብሩክ የፍቅረኛውንና የልጁን ህይወት ለማዳን መከራውን ያያል። መስፍን በባህርይው ህገወጥ ነገር አይወድም። ለሃገሩ በጎ ነገር ይመኛል። ሚዛናዊ ነው። እልኸኛ ሲሆን፣ ፈሪ አይደለም። ቤተሰቡን ይወዳል። የፕሮፌሰር መስፍንን ሰብእና ለመቅረፅ የታሰበ ይመስላል።
የወያኔ ድርጅታዊ አሰራሮች በድራማው በብዙ ቦታ ተጋልጠዋል። ለአብነት ማህሌት ህገወጥ ተግባር እንድትፈፅም ያደረጋት ራሱ አስናቀ ነበር። መልሶ ግን ማስረጃውን ለግል ጥቅሙ በማዋል ማህሌት እንድትንበረከክለት ለማድረግ ሲሞክር ይታያል። ወያኔ እነ አባዱላን ወንጀል እንዲሰሩ ካደረገ በሁዋላ መልሶ እንደፈለገ የሚጠቀምባቸው በዚሁ መንገድ ነበር። እንደ ማህሌት በየዋህነት የፈፀሙት ወንጀል እንዳይጋለጥባቸው ሲሉ፣ ለህወሃት እየሰገዱ ለመኖር የተገደዱ በርካታ ባለስልጣናትን አውቃለሁ።
ልኡል (የአስናቀ ወንድ ልጅ) ከህወሃት የተወገዱት የህወሃት አመራር አባላት ወኪል ነው ተብሏል። ልኡል የህወሃት ወኪል ልጅ ቢሆንም፣ የስርአቱን ህገወጥ ድርጊት በመቃወም ወደ ሰፊው ህዝብ ጎራ ተቀላቅሎአል። የልኡልና የመስፍን ውይይቶች በጠቅላላ የህወሃትን አካሄድ በሚቃወሙ የህወሃት አባላትና በተቃዋሚ ሃይላት መካከል ያለውን ግንኙነት እንዲጠቁም ተደርጎ ተቀርፆአል። በርግጥ ደራስያኑ ይህን ስለማሰባቸው የሚታወቅ ነገር የለም። የተደራስያን መብት የሚባል ነገር ግን አለ። በተለይ አፈና ባለበት ስርአት ውስጥ የሚኖር ተደራሲ ማንኛውንም የጥበብ ስራ ከወቅታዊ አስተሳሰቦች ጋር ለማመሳሰል ጥረት ማድረጉ የተለመደ ነው።
የገፀባህርያቱ ዝርዝር ውክልና ሳያስገርመኝ አልቀረም። መለስ ብዬ ታሪኩን አንድ ባንድ ሳሰላስለው በትክክልም አሁን ያለውን የፖለቲካ ሁኔታ ፍንትው አድርጎ ሲገልፅ የሰነበተ ድራማ ይመስላል። ድራማው በፍጥነት እንዲቋጭ የተደረገው ፖለቲካዊ ይዘት እንዳለው በመታወቁ ይሆን?
በኔ የግል አስተያየት ድራማው በጥሩ አጨራረስ ተደምድሞአል። ያልተስማማኝ ጉዳይ ቢኖር መዲ ከነልጇ መሞቷ ነው። ፅንስ ሁልጊዜ፣ ከትውልድ መቀጠልና ከተስፋ ጋር የሚዛመድ እንደመሆኑ፣ ክስተቱ ተስፋን የሚገድል ሆኖብኛል። ማህሌት እንደ ኢትዮጵያ ወኪልነቷ የልጅ ልጇን ማየት ነበረባት። በእርግጥ ድራማው ያለቀው ብሩክ ከመሰደዱ በፊት መሆኑ የድራማው ጠንካራ ጎን ነው። ድራማው ከማለቁ በፊት ብሩክ በቁጣ ወደ ፍቅረኛው እናት ሲራመድ አይተናል። ይህ የብሩክ እንቅስቃሴ ህዝብ ሲቆጣ ሊፈፅም የሚችለውን የመጨረሻ አደገኛ ሁኔታ የሚጠቁም ሆኖ ታይቶአል። የመድሃኒት እናት ልጇን የገደለችው ባለማወቅ ነው። ይህች ሴት የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ወኪል ትመስላለች። ባለማወቅ የራስ ጥቅም ላይ ጥይት መተኮስ።
ድራማው ያላለቀ ቢመስልም በጥሩ ሁኔታ ተደምድሞአል። ርግጥ ነው ሟቾች በዝተዋል። በለውጥ ወቅት መስዋእትነት የሚጠበቅ ነው። ተወዳጁ ገፀባህርይ መስፍን በመጨረሻ ድል ማድረጉ ተስፋ ነው። የኢትዮጵያ ተምሳሌት ሆና የሰነበተችው ማህሌት በጭንቀትና በፍርሃት እንደተዋጠች ድራማው ማለቁ በትክክልም አሁን ኢትዮጵያ ያለችበትን አስጨናቂ ሁኔታ ይጠቁማል። የአስናቀ አወዳደቅ የህወሃትን የመጪው ዘመን እጣ ፈንታ ያመላክታል።
በረከትና መለስ ድራማው ገብቶአቸው ከሆነ ብዙ ሊማሩበት ይችላሉ። ኢህአዴግ 99.6 % በመቶ የኢትዮጵያ ህዝብ ደጋፊዬ ነው እያለ የራሱን ድምፅ ይሰማል። ከእለታት አንድ ቀን አዳራሹን ሲከፍቱት ግን ባዶ ሆኖ ያገኘዋል። በመጨረሻ ደራስያኑን አድንቄያለሁ። በመቀጠል መሪ ተዋንያኑ ሊመሰገኑ ይገባቸዋል። ዳይሬክተሩና የድምፅ ባለሞያው፣ ወደር የላቸውም። የጥበብ አምላክ ሌላ ብዙ ያፈልቁ ዘንድ ያግዛቸው።

No comments:

Post a Comment