"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Wednesday 11 July 2012

ወንጀለኛው የመለስ አጃቢ


– (ከኢየሩሳሌም አርአያ)


ከኢትዮ ሚዲያ የምርመራ ዝግጅት ክፍል ጋር በመተባበር ሕወሐት/ኢሕአዴግን የሚመለከቱ መረጃዎች በተከታታይ ይቀርባሉ። የዛሬው ጥንቅር እነሆ፦
አቶ መለስ ዜናዊ በሚደረግላቸው የተጠናከረ ልዩ የጥበቃ እንቅስቃሴ ውስጥ አዘውትሮ የማይጠፋ ሹም አለ። መለስ ከቤተ መንግስት ሲወጡም ሆነ ሲገቡ ከሚንፈላሰሱባቸው አሜሪካ ስሪት ዘመናዊ ካዲላኮች ፊት ለፊት ነጭ የፖሊስ ሞተር ሳይክል መንገዱን እየመራ ይጏዛል። ብዛት ያላቸው ሞተረኞች ከጎንና ጎን ሆነው ይከተላሉ።
መልኩ ጥቁር፣ፀጉሩ ከርዳዳ፣ጥቁር መነፅር የሚያዘወትር፣ፊቱ የማይፈታና አስፈሪ ነው። ሲናገር ቁጡና ድምፀ ጎርናና ነው። ሻምበል ታዬ ኡርጂ ይባላል። በደርግ ዘመን መቶ አለቃ የትራፊክ ፖሊስ ሞተረኞች ዋና አዛዥ፣ በመሆን በሁለቱ ስርአት ሁለቱንም መሪዎች እያገለገለ ይገኛል።
ፈረንሳይ ለጋሲዮን ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ከፍተኛ 12 ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ጀርባ የገነባው መኖሪያ ቤት ይገኛል። ሰኔ 1990 ዓ .ም ሻምበል ታዬ እስር ቤት እንዲገባ ተደረገ። ከታላቁ ደራሲ በአሉ ግርማ ግድያ ጋ በተያያዘ «እጁ አለበት» ተብሎ ነበር የታሰረው። የደርግ ባለስልጣናትን ጉዳይ ይመለከት በነበረው የስድስት ኪሎ ጠ\ፍርድ ቤት እንዲቀርብ ተደረገ።
«ቀኑና አመቱን በውል አላስታውሰውም» ሲል ለችሎቱ ንግግር የጀመረው ተከሳሹ፣ የቃሉ አጠቃላይ ጭብጥ ሲጨመቅ ይህን ይመስል ነበር።

“ በምሽት ለአስቸኳይ ስራ ትፈለጋለሕ ተብሎ ከቤተመንግስት ሹማምንት መልእክት ይደርሰዋል። መንግስቱ ሃ/ማሪያምን ለማጀብ በሚገለገልባት ላንድሮቨር የፖሊስ መኪና ፈጥኖ በግቢው ይደርሳል። ዝግጁ ሆነው ይጠብቁ የነብሩ የታጠቁ ወታደሮች ፊታቸውን እንደተሸፈኑ በታዬ መኪና ይጫናሉ። ራዲዮመገናኛ የጨበጠ አለቃቸው ወደ ጊዮርጊስ አቅጣጫ እንዲጔዝ ይነግረዋል።
በእሳት አደጋ ቢሮ ዳገቱን ወጥተው ወደ ቀኝ የስድስት ኪሎ መንገድ አቅጣጫ ከታጠፉ በኋላ በአካባቢው ካሉ ግሮሰሪዎች በአንዱ ትይዩ ቆሙ። ወታደሮቹ በፍጥነት ወደ መጠጥ ቤቱ አምርተው ሲያበቁ፣ አፍታም ሳይቆዩ አንድ ግለሰብ የፊጥኝ በካቴና አስረው ፣ እየጎሸሙና እየገፈታተሩ መኪናው ላይ ጫኑት። በፒያሳ፣ቸርችል ጎዳና እያቆራረጡ ወደ ጎተራ አቅጣጫ በፍጥነት ከነፉ። ዮሴፍ ቤ/ክርስቲያንን እንዳለፉ ጥግ ይዘው ቆሙ። ጨለማ ውስጥ ቆማ ትጠብቅ ወደነበረችው መኪና ወታደሮቹ እስረኛውን ይዘው ገቡና ወደ ቃሊቲ አቅጣጫ ከነፉ።”
«የወታደሮቹ አለቃ ተመለስ ብሎ ባዘዘኝ መሰረት ያንኑ ፈፀምኩ» ያለው ተከሳሹ – ታፍኖ የተወሰደው ግለሰብ በዓሉ ግርማ መሆኑን ያወቀው ካለፈ በኋላ መሆኑን ገለፀ። ለአቃቤ ሕግ መስቀለኛ ጥያቄ ያልተበገረው ተከሳሽ የአፋኞቹን ማለትም የገዳዮቹን ማንነት ለይቶ እንደማያውቅና ፊታቸውን እንደተሸፈኑ በመግለፅ፣ ከላይ የተቀመጠውን ብቻ እንደሚያውቅ ተናገረ።
አንድ አመት ወህኒ በእስር የቆየው ይህ ግለሰብ ያለ ፍ\ቤት ውሳኔ ዛሬም ድረስ እንቆቅልሽ በሆነ መልኩ ከእስር እንዲለቀቅ ተደረገ። እንደተፈታ የሞተረኞች አዛዥ፣ የመለስ ዜናዊ ዋና አጃቢ ተደርጎ ከመሾሙ በተጨማሪ በአናቱ የሻምበል ማዕረግ ተመረቀለት።
ሻምበል ታዬ ለደርግ ያውም ለመንግስቱ ሃ/ማሪያም ቅርብ የነበረ፣ በታማኝነቱ አጃቢ ሆኖ የተመደበና የቤተመንግስቱ ምስጢር ጠባቂ አባል ሆኖ ሳለ፣ የበአሉ ግርማን ገዳዮች አላውቃቸውም፣ አይኔን ግንባር ያድርገው ማለቱ አልበቃ ብሎ በሌላ መኪና እንደወሰዱት አድርጎ መዘላበዱ ውሀ የማይቋጥር ክሕደትና ሸፍጥ ነው ይላሉ – ጉዳዩን በቅርብ የተከታተሉ ታዛቢዎች። ቤተመንግስት ተጠርቶ በአሉን ለማፈን ትዕዛዝ ተቀብሎ የተሰማራው ለስርዓቱ የበለጠ ታማኝ፣ ቅርብና ምስጢር ጠባቂ ሁኖ በመገኘቱ ነው ሲሉ አስተያየታቸውን ያጠናከሩት እነዚህ ወገኖች አክለውም፦ ደርግ ማንን ፈርቶ ነው ሁለተኛ መኪና የሚመድበው? በማለት ይጠይቃሉ። ጉዳዩን ይከታተሉ የነበሩ ዓቃቤ ሕግ የሻምበል ታዬ መፈታት እንቆቅልሽ እንደሆነባቸውና ከወንጀሉ ነፃ ሊያደርገው የሚችል ምንም አይነት ማስረጃና መከላከያ ያለማቅረቡን ተናግረዋል። የሕግ ባለሙያው ይህን ሲናገሩ አሁን የኢሕአዴግ ባለስልጣን የሆነው ሽመልስ ከማል (በወቅቱ የጋዜጣ አዘጋጅ)ጭምር አብሮን እንደነበረ መጠቆም እወዳለሁ። የበአሉ ግርማ ደም ከሚጮህባቸው አንዱ ሻምበል ታዬ ኡርጂ ነው ሲሉ አቃቤ ሕጉ ያስረግጣሉ።
( የሆነስ ሆነና አሜሪካ የመሸጉት ሰውዬ ከበአሉ ግድያ ጋ በተያያዘ አብሮ ስማቸው ይነሳል። እንዲያውም በአንድ ወቅት በጋዜጣ ስማቸው ተጠቅሶ ሲወነጀሉ ነበር። ጉዳዩን የሚያውቁ ጋዜጠኞች «ዝም ጭጭ» ብለዋል። እስከመቼ?….)
ማጠቃለያ፦ አቶ መለስ ዜናዊ ብዙ ጊዜ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን «የደርግ/ኢሰፓ ጥርቅሞች፣ወንጀለኞች» ወዘተ እያሉ በአደባባይ ሲናገሩ ይደመጣሉ። የእርሳቸው አጃቢ ሻምበል ታዬ የጀርባ ወንጀል ታሪክ በጉያቸው ሸሽገው ወደ ሌሎች ጣት መቀሰራቸው እጅግ ያሳፍራል። ለነገሩ በመለስ መዳፍ የበርካታ ኢትዮዽያውያን ደም ስለሚጮሕ የበአሉ ግርማ ጉዳይ ብዙም ባያስጨንቃቸው አይገርምም።
ሌላው የሻምበል ታዬ ገመና የለየለት ሙሰኛ መሆኑ ነው። ፒያሳ ዶሮ ማነቂያ ተብሎ በሚጠራው ከባቢ « በቀለ ስጋ ቤት» በየወሩ ዕቁብ ይሰበሰባል፤ እስከ አራት መቶ ሺህ ብር ነው የሚጣለው። ለታዬ በየወሩ የእቁብ ሒሳብ የሚከፍሉት የታክሲ ባለንብረቶች ናቸው። ሙስናው አገር ያወቀው፣ፀሐይ የሞቀው ነው።
በሚቀጥለው መለስ ዜናዊ በረቀቀ መንገድ ስላስገደሏቸው ባለስልጣናት እና ስለ አደገኛው የሻዕቢያ ተላላኪ በተከታታይ መረጃዎችን ይዘን እንቀርባለን።


No comments:

Post a Comment