"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Wednesday 27 June 2012


ሰበር ዜና፡- ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና ሌሎች ተከሳሾች ጥፋተኛ ተባሉ






በእነ አንዷለም አራጌ መዝገብ በሽብርተኛነት ተጠርጥረው በፌደራል ዓቃቤ ሕግ ክስ የተመሰረተባቸው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን ጨምሮ 24 ተከሳሾች ሰኔ 20 ቀን 2004 ዓ.ም. ጥፋተኛ ተባሉ፡፡
ክሱን ሲመረምር የቆየው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሦስተኛ ወንጀል ችሎት ጥፋተኛ ያላቸው አንዷለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ ዮሐንስ ተረፈ፣ የሽዋስ ይሁንዓለም፣ ክንፈሚካኤል ደበበ፣ ምትኩ ዳምጤ፣ እስክንድር ነጋና አንዱዓለም  አያሌው በማረሚያ ቤቱ ሲገኙ፣ የተቀሩት በሌሉበት ጥፋተኛ ተብለዋል፡፡

eskinder nega fente
ተከሳሾቹ የተመሠረቱባቸውን ስድስት ክሶች ባለመከላከላቸው የጥፋተኝነት ውሳኔ ማስተላለፉን ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡
ዓቃቤ ሕግና ተከሳሾች የቅጣት ማክበጃና ማቅለያ ሐሳብ እንዲያቀርቡ ተጠይቀው፣ ዓቃቤ ሕግ በሰጠው የቅጣት ማክበጃ አስተያየት ተከሳሾች እንደተመሠረተባቸው የክስ ዓይነት ከአምስት ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ ጽኑ እስራት እንዲቀጡለት ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
በሌሉበት ከተከሰሱት መካከል ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ከዚህ በፊት የዕድሜ ልክ እስራት ተፈርዶባቸው በይቅርታ የተፈቱ ቢሆንም፣ በተመሳሳይ ወንጀል ተግባር ላይ መሳተፋቸው ጥፋቱን ተደራራቢ ስለሚያደርገው፣ ከሞት ቅጣት ዝቅ ብሎ የቅጣት የመጨረሻ ጣሪያ በዕድሜ ልክ እንዲቀጡ ዓቃቤ ሕግ ጠይቋል፡፡ አቶ አንዷለም አራጌም በተመሳሳይ ተደጋጋሚ የወንጅል ድርጊት በመገኘታቸው በዕድሜ ልክ እንዲቀጡ ዓቃቤ ሕግ ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካይነት የቅጣት ማቅለያ ሐሳባቸውን እንዲያቀርቡ ሲጠይቅ፣ ጠበቆቹ በተደጋጋሚ ማረሚያ ቤት ተገኝተው ደንበኞቻቸው የቅጣት ማቅለያ አስተያየት እንዲሰጧቸው ቢጠይቋቸውም የቅጣት አስተያታቸውን ራሳቸው እንደሚያቀርቡ መግለጻቸውን አስረድተዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ ለራሳቸው በሚጠቅም መንገድ የቅጣት ማቅለያ ሐሳብ እንዲያቀርቡ በማሳሰብ የመጀመሪያውን ዕድል ለአቶ አንዷለም አራጌ ሰጠ፡፡ አቶ አንዱዓለም ባቀረቡት የቅጣት ማቅለያ ሐሳብ እንደገለጹት፣ ባለፈው ግማሽ ምዕተ ዓመት የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሰላምና ለዲሞክራሲ ትግል ያደረገበት ጊዜ ነው ብለው፣ ‹‹እኔም ለልጆቼ፣ ለወገኖቼ፣ ለአገሬና ለራሴ በመረጥኩት ሰላማዊ ትግል ስታገል ቆይቻለሁ፡፡ የበደልኩት ሕዝብ አለ ብዬ አላምንም፡፡ ወንጀል ሠርቻለሁ ብዬ አላስብም፡፡ ውስጤ ፍጹም ሰላማዊ ነው፡፡ ከሳሾቼ የሚሰጡኝን የግፍ ፅዋ ለመጠጣት ዝግጁ ነኝ፤›› ሲሉ፣ ፍርድ ቤቱ አስቆማቸው፡፡ እሳቸውም በቃኝ ብለው አቆሙ፡፡
ፍርድ ቤቱ ሌሎች ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካይነት የቅጣት ማቅለያ ከሚቀጥለው ቀጠሮ በፊት እንዲያቀርቡ ያዘዘ ሲሆን፣ ተከሳሾቹ የእነሱ ሐሳብ እንዲሰማ በማለት ዓቃቤ ሕግ እንደተሰማው እኛም እንሰማ ብለው ነበር፡፡ ነገር ግን ፍርድ ቤቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ያወጣው የቅጣት አወሳሰን ማኑዋል የቅጣት ማቅለያ እንዴት መቅረብ እንዳለበት እንደሚያዝ አስታውሶ፣ ተከሳሾቹ በዚያ መሠረት ከውሳኔ በፊት የቅጣት ማቅለያ ሐሳባቸውን እንዲያቀርቡ አዞ፣ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ለሐምሌ 6 ቀን 2004 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው ክስ ተመሥርቶባቸው ጥፋተኛ የተባሉት ተከሳሾች ከአንድ ዓመት በላይ በእስር ላይ መቆየታቸው ይታወሳል፡፡ በእነ አንዷለም አራጌ የክስ መዝገብ ክስ የተመሠረተባቸው ተከሳሾች በተወካዮች ምክር ቤት አሸባሪዎች ተብለው ከተሰየሙ ድርጅቶች ጋር በመተባበር፣ ከኤርትራ መንግስት ወታደራዊና የፋይናንስ ድጋፍ በማግኘት፣ ሕገ መንግሥታዊውን ሥርዓት በኃይል ለመጣል አማራጭ ያስቀመጠው ግንቦት 7 ቡድን አመራርና አባል በመሆን የአገሪቱን ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሕገ መንግሥታዊ ተቋማት ለማናጋት በማሰብ፣ የድርጊቱን ዓላማና ግብ ሙሉ በሙሉ በመቀበል ተሳትፎ አድርገዋል ተብለው መከሰሳቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡




No comments:

Post a Comment