"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Wednesday 13 June 2012

የ‹‹አራት ኪሎው›› እና ‹‹የቃሊቲው መንግስት›› ወግ


የ‹‹አራት ኪሎው›› እና ‹‹የቃሊቲው መንግስት›› ወግ




ተመስገን ደሳለኝ
ሲሳይ አጌና በቅርቡ በመጀመሪያ በጀርመን፣ ቀጥሎ በአሜሪካን ሀገር ‹‹የቃሊቲው መንግስት›› የሚል ርዕስ ያለው መፅሐፍ አሳትሟል። በእርግጥ መፅሐፉ እስከአሁን ሀገር ቤት መግባት አልቻለም (ምናልባት ወደፊትም ላይገባ ይችላል)
ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና በኢትዮጵያ የነፃ ፕሬስ ታሪክ የጎላ አሻራ ካላቸው ጥቂት ጉምቱ እና ትንታግ ጋዜጠኞች አንዱ ነው። ከ1986 ዓ.ም. ጀምሮ በድህረ ምርጫ 97 በተነሳው አለመግባባት ስራ እስካቆመበት ዕለት ድረስ ‹‹ኢትኦጵ›› እና ‹‹አባይ›› የተባሉ ጋዜጦችን በባለቤትነት ይመራ ነበር። በተለይ ኢትኦጵ ጋዜጣ በእጅጉ ተወዳጅ ከመሆኗም ባሻግር በስርጭትም ግንባር ቀደም እንደነበረች ይታወሳል።
ጋዜጠኛ ሲሳይ ከቅንጅት መሪዎች ጋር አብሮ ታስሮ ነበር። የተለቀቀውም ልክ እንደእስክንድር ነጋ ፍርድ ቤቱ ‹‹ነፃ ነህ›› ብሎት ነው፡፡ ይህ አንድ እውነት ቢሆንም ብሮድካስት ኤጀንሲ የተባለ ‹‹ፍቃድ ሰጪ እና ፍቃድ ነሺ›› መስሪያ ቤት ወደ ፕሬሱ እንዳይመለስ በመከልከሉ ዛሬ በአሜሪካን ሀገር በስደት ይኖራል። ‹‹የቃሊቲው መንግስት›› የሚል ርዕስ የሰጠውን መጽሐፉንም ያሳተመው በዛው በስደት አለም ነው። (በነገራችን ላይ ይህ ፅሑፍ የመፅሐፉ ዳሰሳ /Book review/ ባለመሆኑ ስለመፅሐፉ ይዘት፣ ጠንካራ እና ደካማ ጎን አንነጋገርም። የምንነጋገርበት አብይ ጉዳይ በመጽሐፉ ላይ ስለተገለፀው የፍትህ ስርዓቱ ሹቀት፣ የፀጥታ አስከባሪዎች ገለልተኛ ያለመሆን፣ ስለእስረኛ አያያዝ እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ብቻ ነው። ይህንን መንገድ የመረጥኩበት አንዱ ምክንያት የሚመለከተው ክፍል ቢያንስ በዋና ዋና ጉዳዮቹ ላይ መልስ ይሰጥበታል በሚል ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ከመጋረጃው ጀርባ ያለውን የኢህአዴግን ፖለቲካ ‹‹ፈገግ›› በሚያደርጉ ገጠመኞች ታጅበን ለማየት እንዲያስችለን ነው) በቅድሚያ ሲሳይ አጌና ይህንን መፅሐፍ ለምን እንዳዘጋጀ በመግቢያው ላይ ከገለፀው ጨርፈን እንይ፡-

‹‹…ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ወዲህ በዚሁ የፕሬስ ሥራ ሳቢያ ለ6ኛ ጊዜ መታሰሬ ነው። ይህንን እንደ ገድል ልዘክረው ያነሳሁት ሳይሆን፣ የነፃው ፕሬስ ባልደረቦች ‹ሕዝብና መንግስት በማጋጨት›፣ ‹ሕዝብን ለአመፅ በማነሳሳት› እየተወነጀልን ስንታሰር ስንፈታ መኖራችንን በማስታወስ፤ በእስር ቤቱ ‹ደንበኝነቴ› የሰበሰብኳቸውን መረጃዎች በመጽሐፉ ውስጥ በየአጋጣሚው ስለሚነሳ ይህን በሰሚ ሰሚ የቃረምኩት ሳይሆን፣ ራሴ ያለፍኩበትና ከምንጩ በቀጥታ የተቀዳ መሆኑን ለማረጋገጥ ነው። እርግጥ ነው ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ከበደ፣ ጋዜጠኛ መኮንን ወርቁ፣ ጋዜጠኛ ታምሩ ተስፋዬ የተባሉ የነፃው ፕሬስ ባልደረቦች ራሳቸውን እስከማጥፋት የዘለቁበትን አስጨናቂ ሂደት ማለፋችንንም መግለፅ ራሱ ስለነፃው ፕሬስ ፈተና ብዙ ይናገራል። ከእነዚህ ሶስቱ ጋዜጠኞች
አንዱ መኮንን ወርቁ በፖሊስ ያልተቋረጠ ክትትል በመማረርና በሌላ የፕሬስ ክስ ዋሱ የነበሩት ሰው በመታሰራቸው በሞቱ ነፃ ሊያወጣቸው በራሱ ላይ ዕርምጃ የወሰደ ሰማዕት ነው።›› የፈጣሪ ያለህ! ምን ያህል አስጨናቂ ጫና ቢሆን ነው ራስን እስከማጥፋት የሚያደርሰው?
ይህ መጽሐፍ የሚያተኩረው በይበልጥ በድህረ ምርጫው ‹‹ጦስ-ጥንቡሳስ›› የቅንጅት መሪዎች ከያሉበት ጓዳ ጎድጓዳ ታድነው እንዴት እንደተያዙ፣ ቀጥሎም የእስር አያያዛቸው እና የፍርድ ቤት ውሎአቸው ምን ይመስል እንደነበረ ነው። በዚህ አጋጣሚም ነው በሀገራችን የፍትህ ስርዓት ላይ ስጋት እንዲገባን የሚያደርጉ አስደንጋጭ እና በቁጣ የሚያነዱ ክስተቶችን ከመፅሀፉ ላይ ያገኘሁት።
ያችን ሰዓት
‹‹መጨረሻው ሲጀመር›› በሚል ርዕስ ፖለቲከኞቹ እና ጋዜጠኞቹ እንዴት ታድነው
እንደተያዙ ተዘርዝሯል። ‹‹ያች ሰዓት›› (ጥቅምት 22/1998 ከቀኑ 10 ሰዓት በኋላ ጀምሮ ነው) የደህንነት ሀይሎች ለወራት ሲከታተሉና ሲያዋክቡ የቆዩትን ታሳሪዎች አሳደው መያዝ የጀመሩባት። ዕለቷ በአዲስ አበባ ዋና ዋና ቦታዎች ‹‹በምርጫው ኢህአዴግ አጭበርብሮአል›› ያሉ ወጣቶች ዛሬም ድረስ ጥሪው ከማን እንደተላለፈ ተለይቶ ያልታወቀ ‹‹የመብት ጥያቄ››ን በማንገብ በዋና ዋና ጎዳናዎች ላይ ከታጣቂዎች ጋር የተፋጠጡበት የጭንቅ እና የሰቆቃ ሰአት ናት -ያች ሰዓት። በእርግጥ ይህ መጽሐፍ ለጅምላ እስሩ የእለቱ ግጭት ብቻ ምክንያት እንዳልሆነ ይሞግታል። እንደ ምክንያት የሚያስቀምጠውም ቅንጅቱ መስከረም 22/1998ዓ.ም ‹‹ከቤት ውስጥ ያለመውጣት›› አድማ እንዲደረግ ያስተላለፈውን ጥሪ በዋዜማው በዲፕሎማቶች ጫና ከሰረዘው በኋላ፣ በእለቱ በታላቁ ቤተ-መንግስት ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ዲፕሎማቶቹ ባሉበት በተደረገ ውይይት ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በእንግሊዘኛ ቋንቋ ‹‹ቤት የመቀመጥ ጥሪውን ባትሰርዙት ኖሮ ጋዜጠኞችን ጨምሮ ሰብስቤ ላስራችሁ ነበር›› ያሉትን በመጥቀስ ነው። እንግዲህ ምንም አይነት የጎዳና ላይ ነውጥ ሊቀሰቀስ የማይችል የትግል ጥሪ ያስተላለፉ ሰዎች ሊታሰሩ ተወስኖ ከሆነ ልክ በወሩ ‹‹ህገ መንግስቱን በኃይል ሊንዱ ነው›› ተብለው የታሰሩበትን መንግስታዊ ምክንያት ያፋልሰዋል ማለት ነው። (የመጽሐፉ ደራሲ ሊያስሩት ከመጡ የፀጥታ ሰራተኞች አምልጦ ለአንድ ወር ከተደበቀበት ተይዞ ወደ ማዕከላዊ ፖሊስ ጣቢያ ሲሄድ ያጋጠመውን ፈገግ የሚያሰኝ ሁኔታ ደግሞ እንዲህ ሲል ይጨምርልናል፡-
‹‹…ሹፌሩ ከመስቀለኛው መንገድ በቀጥታወደ ግራ መታጠፍ ሲገባው ወደ ቀኝ ታጥፎ የአዲሱ ገበያን መንገድ ተያያዘው። በመገረም ወዴት እየወሰደን ነው? በማለት ከራሴ ጋር ስሟገት እንደገና
ወደ ግራ ታጥፎ ቁልቁል የጊዮርጊስን መንገድ ያዘ፡፡ ወደ ማዕከላዊ ምርመራ ማስተባበሪያ ይገባል
ብለን ስንጠበቅ ቁልቁል ሸመጠጠ። በመኪና ውስጥ ያጀቡን አራት መሳሪያ ያነገቱ ፖሊሶችና አንድ ከሹፌሩ ጎን የተቀመጠው ኃላፊያቸው እንዲሁም ሹፌሩ ማዕከላዊ ምርመራ የቱጋ እንደሆነ በትክክል እንደማያውቁ የተገነዘብኩት ይሄኔ ነበር። ግራ በመጋባት የትኛው ነበር እያሉ ሲጠያየቁ መኪናውን አዙረው እንዲመለሱ የነገርኳቸውና የምታሰርበትን ግቢ ያሳየኋቸው እኔው ራሴ ነበርኩ።›› መቼም ይህ በእጅጉ የሚደንቅ ነው። በአዲስ አበባ ከተማ የሚኖሩ ፀጥታ አስከባሪዎች ‹‹ለፀጥታው አስጊ›› ያሏቸውን ሰዎች አድነው ከያዙ በኋላ የሚያስሩበትን ዋነኛ ቦታ አለማወቃቸው በወቅቱ ‹‹የተባበሩት መንግስታት ሰላም አስከባሪ ሰራዊት›› ጣልቃ ገብቶ ነበር እንዴ? ብለን እንድንጠይቅ ያደርገናልና።
እስር ቤቶቹ
ጠዋት እና ማታ ወደ መፀዳጃ ቤት ብቻ መሄድ እንደሚቻል ፈቅዶ የቀረውን ሙሉ ሌሊት እና ሙሉ ቀን በተቆለፈ በር ውስጥ ከመገደቡ ውጭ የማዕከላዊ እስር ቤት ከሌሎቹ የሀገሪቱ እስር ቤቶች የተሻለ እንደሆነ ይነገራል። ‹‹የቃሊቲው መንግስት›› መፅሐፍም ይህንን ያረጋግጣል።
ከዚህ ውጭ የቃሊቲው ማረሚያ ቤት ‹‹የምድር ሲኦል›› ነው፡፡ የመጽሐፉ ትርክት ደግሞ እስር ቤቱን ከሲኦልም በላይ የከፋ አድርጎ ገልፆልን ሲያበቃ፣ ስቃዩን ይበልጥ በመከራ የተመረገ የሚያደርገው ማረሚያ ቤቱን የሚያስተዳድሩት የፌደራል ፖሊስ አባላት ለገዥው ፓርቲ የወገኑ
መሆናቸው እንደሆነ ይገልፃል። ‹‹ፖሊስ ገለልተኛ ነው›› የሚባለውም በወረቀት እንጂ በተግባር በግልባጩ ነው ሲልም ያረዳናል። ወይም የምናውቀውን ሃቅ ያረጋግጥልናል።
በእርግጥ ትርክቱ በደረቁ አይደለም። ምክንያታዊ ነው። ለምሳሌ ታህሳስ 26/1998 ዓ.ም. ጋዜጠኞቹ እና የጋዜጣ አሳታሚ ድርጅቶቹ ባለቤቶች ፍርድ ቤት ሲቀርቡ በመመካከር ሁሉም ‹‹ጥቁር ቲሸርት›› ለብሰው የህሊና እስረኞች እንደሆኑ ለማሳየት ጥረት አደረጉ። ሙከራቸውም ተሳክቶ ድርጊቱ የዜና ሽፋን አገኘ። ሆኖም ማረሚያ ቤቱ የእስረኞቹን ሻንጣ ፈትሾ ጥቁር ቲሸርት የተባለ እንዲወረስ ከማድረጉም በላይ ከዚያን ዕለት ጀምሮ ከቤተሰብ፣ ለእስረኞቹ ጥቁር ቲሸርት እንዳይገባ ከልክሏል፡፡ ይህ አንዱ ማሳያ ነው። አፍንጫ ሲመታ… ሌላው ይቀጥላል።
‹‹በዚያ 250 ያህል ሰው በሚይዘው አዳራሽ ውስጥ ደስታ፣ መሐሪ፣ ለገሰ፣ አባስ፣ ኃይሉ የሚባሉ የአእምሮ በሽተኞች ያሉ ሲሆን፣ ጆንሰን የሚባለው ሱዳናዊ ወፈፌ ሲጨመር 6 የአእምሮ በሽተኞች ከእኛ ጋር ይኖራሉ።›› ይልና በሌላ ገፅ ላይ ደግሞ በትክክል ተቆጥረው ሃምሳ የሚሆኑ የሳምባ በሽተኞች በዚሁ ክፍል እንዲገቡ መደረጉ ለጤና አደገኛ በመሆኑ ለፍርድ ቤቱ እስከማመልከት ቢደረስም የተገኘ ለውጥ እንደሌለ ያትታል።
እዚህ ላይ አጥንት ድረስ ሰርስሮ ከሚገባ ሀዘን ጋ የሚያላትመን መሀሪ እና አባስ፣ እንዲሁም አማርኛ መናገርም ሆነ ማንበብ የማይችለው ከቤንሻንጉል ስራ ፍለጋ የመጣው (ስሙ ያልተጠቀሰ) ታሳሪን ጨምሮ ሶስቱም የአእምሮ በሽተኛ የሆኑት ሚያዝያ 10 ቀን 1993 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ በተነሳው አመፅ ተይዘው ‹‹ህገ መንግስቱን በኃይል በመናድ እና በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ውድመት በማስከተል›› የሚል ክስ ሲቀርብባቸው ደንግጠው መሆኑ ነው። መሀሪ ስራ ፍለጋ ከጎንደር የመጣ ሲሆን፣ አባስ ደግሞ ጫማ በመጥረግ የሚተዳደር ሊስትሮ ነበር። ሲሳይ የቤንሻንጉሉ ወጣት አማርኛ አለመቻሉን ጠቅሶ እንዲህ ይላል ‹‹ከእነአባስ ጋር በምን ቋንቋ መክሮ በወንጀሉ ተባባሪ እንደሆነ የሚያውቀው ዐቃቢ ህግ ብቻ ነው››
የሀገራችንም ሆነ አለም አቀፍ ህጎች ስለእስረኛ አያያዝ ደንግገዋል። እናም በምንም መልኩ በትንፋሽ በሚተላለፍ በሽታ የተያዙ እና የሚያደርጉትን የማያውቁ የአእምሮ ህሙማን ከጤነኛ ጋር መታሰራቸው ለማንም ሰው አደገኛ መሆኑ አይጠፋውም። የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ሀላፊዎችን ጨምሮ። መቼም ታሳሪዎቹ ‹‹ምርኮኛ›› ናቸው የሚል የለም። ለነገሩ ምርኮኛም ቢሆኑ በእንዲህ አይነት ሁኔታ እንዳይታሰሩ ህጉ በበቂ ሁኔታ ይከለክላል። የሲሳይ አጌና ‹‹ፖሊስ ገለልተኛ አይደለም›› መከራከሪያም ከብዙ ጥቂቱ ይህ ነው። በእርግጥ ይህ ጥያቄ የእኔም ነው። ፖሊስ ገለልተኛ ከሆነ ከገዥው ፓርቲ ጋር በሃሳብ የተኳረፈን እስረኛ ስለምን በእንዲህ አይነት አደገኛ ጥቃት ይበቀላል? መልስ የሚያስፈልገው ነው። ምናአልባትም የአንዱአለም አራጌን ከሌላ ክፍል ተቀይሮ በመጣ እስረኛ መደብደብ ከዚህ ጋር እያነፃፀርን አብዝተን ልንጠረጥር እንችላለን። አሊያ ህገ መንግስቱ የተናደው በታሳሪዎች ሳይሆን በአሳሪዎች ነው የሚለውን ዛሬም ድረስ በህይወት ያለን መከራከሪያ አጥብቀን እንድንይዝ እንገደዳለን።
ማነው መንግስት?
ሲሳይ አጌና ለመፅሐፉ ‹‹የቃሊቲው መንግስት›› የሚል ርዕስ የሰጠው የቅንጅት መሪዎች ቃሊቲ በታሰሩበት ወቅት ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ምዕራባውያን ባለስልጣናት በሙሉ በአራት ኪሎ ቤተመንግስት ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ጋር ከተወያዩ በኋላ፣ በቀጥታ ወደ ቃሊቲም ሄደው ከታሳሪዎቹ ጋር መወያየታቸው የተለመደ ተግባር መሆኑን ያስተዋሉ የወህኒ ቤቱ እድምተኞች፣ የቅንጅት መሪዎችን ‹‹የቃሊቲው መንግስት›› እያሉ መጥራታቸው መጽሐፉን በዚህ ርዕስ እንዲሰይም እንዳደረገው በተዋበው ብዕሩ ይተርካል።
ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት ከአራት ኪሎ እና ከቃሊቲው መንግስት ጋር ተወያይተው ከተመለሱ ባለስልጣናት ውስጥ የአየርላንድ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ የአየርላንድ የውጭ ጉዳይ ሊቀመንበር፣ የአየርላንድ የፓርላማ ቡድን አባላት፣ በወቅቱ በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ሀላፊ ዶናልድ ያማማቶ (በኋላ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ሆነዋል)፣ የአሜሪካ የአፍሪካ ጉዳይ ንዑስ ኮሚቴ ሊቀመንበር እና የአሜሪካ የኮንግረስ አባል ዶናልድ ፔይን፣ ታዋቂው አሜሪካዊው
ምሁር ዶናልድ ሌቪን፣ የአውሮፓ ህብረት የልማትና የሰብዓዊ መብት ኮሚሽነር ሉዊ ሚሽል፣ የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሚስስ ሉዊስ ኦርበር፣ የሲፒጄ (CPJ) ሀላፊዎች… ሲሆኑ፤ አምንስቲ ኢንተርናሽናል፣ የአለም የጋዜጠኞች ፌደሬሽን /IFJ/ እና የአለም የስራ ድርጅት /ILO/ ተወካዮች ደግሞ እስረኞቹን እንዳይጎበኙ ከተከለከሉት ውስጥ ይገኛሉ። በእርግጥም መንግስት ቀን እና ማታ ‹‹ህገ-ወጦች፣ ነውጠኞች፣ አድመኞች፣…›› በሚል ውግዘት በተጠመደበት በዛ ‹‹ክፉ ቀን›› እነዚህ ሁሉ ባለስልጣናት፣ ያውም አስፈሪ አንደሆነ የሚነገርለት ቃሊቲ እስር ቤት ድረስ ሄደው በሀገር ጉዳይ እና በመሳሰሉት ላይ መወያየታቸውን ስናስተውል ለእስረኞቹ የተሰጠው የዳቦ ስም በልክ የተሰፋ ይመስላል-እውነትም የቃሊቲው መንግስት።
ስንት ግራም ማስረጃ?
ሲሳይ በፍርድ ቤት በእሱ እና በፖለቲከኞቹ ላይ የቀረበው መረጃ የኮረኮሩትን ያህል ያሳቀው ይመስላል። የሳቁ መንስኤም ታሳሪዎቹ በቁጥጥር ስር ከመዋላቸው በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሰዎቹ ህግ-ለመጣሳቸው፣ ወንጀል ለመፈፀማቸው ‹‹በቶን የሚቆጠር መረጃ አለን›› ማለታቸውን በችሎቱ ከቀረበው ማስረጃ ጋር አመዛዝኖ ነው። እኛም ወይ ለመሳቅ አሊያም ለማዘን ክሱን እና ማስረጃውን ነጣጥለን እንየው። ክሱ ይቅደም፡-
‹‹ተከሳሾቹ ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ በተሰኘ ድርጅት ስር ተሰባስበው እና አድማ በማድረግ ከጥቅምት 29 ቀን 1997 ዓ.ም. እስከ ህዳር 05 ቀን 1998 ዓ.ም. ባሉት ጊዜያት ከአንድ ጎሳ የመጡ ናቸው በሚሏቸው ላይ ጥቃት በመሰንዘርና በማጥላላት እንዲሁም በኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ ድርጅት አባልና ደጋፊ የሆኑትን ሕዝቡ እንዲያገል አመራር በመስጠት፣ እነዚህን የህብረተሰብ ክፍሎች ለማጥፋት በማሰብና ይህ የወንጀል ድርጊት የሚያስከትለውን ውጤት በመቀበል በሙሉ ሃሳባቸው በመስማማት የጥፋት ድርጊቱ እንዲፈፀም በማደራጀትም ትዕዛዝ በመስጠታቸው በግብረ አበርነት በፈፀሙት የዘር ማጥፋት ሙከራ ወንጀል ተከሰዋል›› ይላል። በአሁኑ ወቅት በሚኒስትር ዲኤታ ማዕረግ የኮምኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤትን የሚመሩት አቶ ሽመልስ ከማል በወቅቱ ዐቃቤ ሕግ ነበሩ። እናም ለዚህ ክስ አስረጅ ይሆነኛል ብለው በችሎቱ ካቀረቧቸው የቪዲዮ፣ የሰነድ እና የሰው ማስረጃ ለአብነት ያህል እንምዘዝ።
የቪዲዮ ማስረጃ ተብለው ከቀረቡት ውስጥ ከአዲስ አበባ ውጭ የቀረበው የደጀን-ደብረማርቆስ እና የአርሲ-አሰላ ህዝባዊ ስብሰባ ብቻ ነው። በደጀኑ ስብሰባ ላይ ከቅንጅት አመራሮች አንዱ የሆኑት አቶ አባይነህ ብርሃኑ፡-
‹‹…ይህቺ ሀገር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከጠመንጃ አገዛዝ ወደ ሰላማዊ መድረክ እንድትሸጋገር ነው የምንታገለው፤ ህዝብ የመረጠው ስልጣን እንዲይዝ›› ሲሉ ተደመጡ። ፊልሙም ቀጠለ
‹‹…አይናችን እንዳያይ፣ እግራችን እንዳይራመድ፣ እጃችን እንዳይሰራ አደንዝዘውናል፤ በሬዲዮ እንደምንሰማው በአደንዛዥ ዕጽ ሊገዙን የፈለጉ ናቸው፤ ከግንቦት 7/97 በኋላ ግን ነፃነታችንን እናረጋግጣለን…›› በማለት የተናገሩ የአንድ ተሰብሳቢ አስተያየትም ታየ፤ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ደግሞ፡ -
‹‹…ሰው ካጠፋ በሕግ ይጠየቃል፤ ዛሬ ግን 10 እና 15 ዓመታት በህግ ሳይሆን በረሐብ እየተቀጣን ነው፤ በአጥንታችን ቀርተናል። በተለይ አማራው እየተቀጣ ነው፤ በአፄ ዮሐንስም በአፄ ምኒሊክም በሁሉም ያጠፋ በህግ ይጠየቃል። በጥፋቱ ይቀጣል፤ የኢህአዴግ ግን የተለየ ነው። በረሃብ ነው የሚቀጣን፤ ዴሞክራሲ እያለ ገበሬውን ጮማ አሳይቶ በረሃብ እየቀጣው ነው፤ ታጣቂዎች ምሽት ምሽት እየመጡ ያሰቃዩናል፤ ቦንብ… ጠመንጃ ይዘሃል እያሉ በራፋችን እየመጡ እያሰቃዩን ነው። እናንተን ስመለከት ደስታ ፈንቅሎኛል፤ የተማሩት የኢትዮጵያ ልጆች መጡልን በማለት ደስታ ተሰምቶኛል፤ ኢትዮጵያ ሰው አጣች ወይ? እል ነበር፤ እርዱን ለአለም አስተዋውቁን…›› ማለታቸውን በችሎቱ ከታየው ቪድዮ ተመልክቷል።ሌላው ቀርቶ ይህ ማስረጃ ሆኖ የቀረበው ፊልም የተቀረፀበት ስብሰባ መሪ አቶ አባይነህ ፊልሙ ታይቶ እንዳለቀ ‹‹የተወነጀሉበት ጉዳይ ምኑ እንደሆነ በመገረም ጠይቀዋል›› ይላል ደራሲው። ከዚህ ውጭ በአዲስ አበባው ስብሰባ ላይ የቀረቡ ቪዲዮዎች በሙሉ በማያወላውል ሁኔታ የትግል ስልቱ ሰላማዊ እንደሆነ አጽንኦት ሰጥተው የተኩራሩበት እንደሆነ ፊልሞቹ ከችሎቱ በቀረቡበት ጊዜ ከታዳሚ ጭምር ተረጋግጧል። አቃቤ ሕግ ደግሞ እነዚህን ፊልሞች እያሳየ ህገ መንግስቱን ለመናድ የተደረገ አደገኛ ሙከራ ነው እያለ መከራከሩን ቀጥሏል። ወደ ሰነድ ማስረጃው እንለፍ።
የሰነድ ማስረጃው በአጠቃላይ 1ሺ 315 ገፅ ነው። ከዚህ ውስጥ በአባላዘር በሽታ የተያዙ ሰዎች የሀኪም ወረቀትም ተያይዞበታል።
‹‹የአባላዛር በሽታ ያለባቸውን ማለትም በሐኪም ሪፖርት ሕመማቸው የአባላዘር በሽታ ስለመሆኑ የሚያስረዳ በማሕተም ተደግፎ በማስረጃነት ቀርቧል። ምናልባት በግርግሩ ሳቢያ አስገድዶ መድፈር ተፈጽሟል በሚል ይሆን ማስረጃው የተያያዘው? በማለት ተጨማሪ የሐኪም ሪፖርቶችን ስንመለከት ሴት ብቻ ሳይሆን የወንድም የአባላዘር በሽተኛ ሪፖርት ተያይዟል፣ የጨጓራና የደም ብዛት በሽተኞችም መንስኤአቸው ቅንጅት ነው ብሎ ዐቃቤ ሕግ አቅርቧል›› ይላል የቃሊቲው መንግስት የተባለው መፅሀፍ። በእጅጉ የሚያስገርመው የሰነድ ማስረጃ ደግሞ ‹‹ፀሎት›› ክስ የሆነበት ነው። እናም ከዚሁ የቅንጅት ክስ ጋር ተያይዞ አራት ሰዎች ለየት ባለ ክስ መከሰሳቸው በመጽሐፉ ተገልጿል። ዐቃቤ ሕግ በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት እንዲደርስ ምክንያት ሆኗል ብሎ ያቀረበው ማስረጃ እንዲህ ይነበባል
ሰኔ 2 ቀን 1997 ዓ.ም.
የሚካኤል ማህበር የእርገት፣ የስለት ዝርዝር
1. አቶ ዳኜ ውበቱ፡- ቤት ከሰራሁና ከነቤተሰቤ በሰላም ከደረስን አንድ ድፎ ዳቦና 2 ጠርሙስ አረቄ
2. አቶ ላቀው ንጋቴ፡- ኢህአዴግ ስልጣኑን በሰላም ለቅንጅት ካስረከበ አራት እንስሳ /ፍየል፣ በግ/ 3 ኪሎ ሽንኩርት
3. መንግስት የያዘውን አቋም ቀይሮ በሰላም ስልጣኑን ለተመረጠው ድርጅት ካስረከበ አንድ ሊትር ዘይት፣ አንድ ኪሎ ጨው እንዲሁም ለበግ መግዣ ተጨማሪ 20 ብር እና የመሳሰሉት ለሚቀጥለው አመት በሰላም ካደረሰን የሚሉ ለፈጣሪያቸው የቀረቡ፣ በአጠቃላይ የአስራ አምስት ምዕመናን የተማፅኖ ድምፆች ናቸው የአመፅ ድምፅ ተብለው በፍርድ ቤት ያውም ህግ በተማረ ዐቃቤ ህግ ፊርማ የቀረቡት።
ከዚሁ ጋር አያይዤ የህገ-መንግስቱን ለመናድ እና ዘር ለማጥፋት የተደረገውን ሙከራ የሚያረጋግጡ ተብለው ከቀረቡት የሰነድ ማስረጃዎች ውስጥ የንግድ ሚኒስቴር የላከውን የዐቃቢ ህግ ማስረጃ ላስነብባችሁ፡-
‹‹…በተቀሰቀሰው አመፅ የእህል ዋጋ ንሯል፣ 310 ብር የነበረው ነጭ ጤፍ 340፣ 280 የነበረው ሰርገኛ ጤፍ 300 ብር መግባቱ፣ 17 ከ50 ሳንቲም የነበረው የቡና ዋጋ 20 ብር መድረሱን እንዲሁም ሽንኩርት፣ ሎሚ፣ በግ፣ በሬ፣ ወይፈን፣ ዶሮ ዋጋቸው መጨመሩ በማስረጃው በዝርዝር ቀርቧል። የጤፍ ዋጋ ከ310 ወደ 340 በመግባቱ እና በአጠቃላይ በዋጋ ንረቱ በአዲስ አበባ ነዋሪ ላይ በወር የ35 ሚሊዮን 610 ሺ ጭማሪ አስከትሏል›› ይላል አቶ መለስ ከክሱ በፊት በቶን የሚቆጠር ሲሉ የተኩራሩበት ማስረጃ። ይሄኔ ነው መሸሽ ያለው ማን ነበር? …የሚገርመው ግን ቅንጅቱ እንዲያ በዛ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ብርሃን አልባ እርችት ሆኖ ብትንትኑ ከወጣ በኋላም የጤፍ ዋጋ በሶስት እጥፍ ለመጨመሩ ህያው ምስክር መሆናችን ነው። ነገር ግን የንግድ ሚኒስቴር እና አቃቢ ህግ ለዋጋ ንረት ያለአንዳች ጥርጣሬ ተጠያቂ መሆን ያለበትን አብዮታዊውን ኢህአዴግ በህግ ሲጠይቁት አላየንም። መቼም ለፍትህ ስርአቱ ነፃ ያለመሆን አስረጅ ከዚህ በላይ የሚያስፈልግ አይመስለኝም።
አሁን ደግሞ ህገ-መንግስቱን በመናድ ለቀረበው ክስ የዐቃቢ ህግ የሰው ምስክሮችን እንይ። ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ከፍተኛ ባለስልጣናቶቻቸውን ለመግደል ቅንጅት አሲሮ እንደነበረ የሰነድ ማረጋገጫ ከኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው ቤት አገኘው በሚል ዐቃቤ ሕግ ላቀረበው ማስረጃ ወረቀቱ ሲገኝ በቦታው እንደነበረ የተናገረ አንድ ‹‹ነጋዴ›› ነኝ ያለ የሰው ምስክርን አቅርቦ አስመስክሯል። ይህ ምስክርም የንግድ ሱቁ ከኢንጅነሩ ቤት ፊት ለፊት እንደሆነና፣ በዚህ አጋጣሚ ፖሊሶቹ በታዛቢነት እንዲመለከት ጠርተውት የተባለው ሰነድ ከኢንጂነሩ ቤት እንደተገኘ መስክሮ ሲጨርስ ኢንጅነር ግዛቸው እንዲህ ሲሉ ጠየቁት፡-
‹‹እርስዎና እኔ የምንተዋወቀው ጠ/ሚኒስትሩ ቢሮ አይደለምን? እኛ ከጠ/ሚኒትስሩ ጋር ለመወያየት መስከረም 22/1998 ቤተ መንግስት ስንገባ እርስዎ ዋና አስፈታሽ አልነበሩም? ባለቤቴ እንዳልፈርም የከለከለችኝ የደህንነቱ ወረቀት ሲቀላቀል አይደለምን? አስፈታሾቹ የመጣችሁትስ በደህንነት መኪና አልነበረም?›› አሉና ኢንጂነሩ ቀጠሉ ‹‹ከእኔ ቤት ፊት ለፊት ሱቅ የለም፤ ፊት ለፊት የቦሌ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ነው›› ያለው ብለው ምስክሩን በችሎቱ ፊት እንዳጋለጡና ምስክሩ የሚመልሰው እንደጠፋው መፅሐፉ ይተርካል።
ነፃነት ደምሴ የአንድ ግብረ ሰናይ ድርጅት የስራ ኃላፊ ሲሆን የተከሰሰው ከቅንጅት መሪዎች ጋር አብረህ አሲረሃል በሚል ከአክሽን ኤዱ ዳንኤል በቀለ ጋር ነው። በነፃነት ላይ ሊመሰክሩ የመጡት ሌላው ምስክር የራሱ የነፃነት ጎረቤት ናቸው። ሲመሰክሩም ‹‹ነፃነት ደምሴ ያነሳሳኝ ስልጣን ከትግሬዎች እጅ መውጣት አለበት በሚል ነው›› አሉና መሰከሩ። ስራቸውም ነጋዴ እንደሆነ አስረዱ። የነፃነት ደምሴ ጠበቃም ምስክሩን የእናታቸው ብሔር ምንድን እንደሆነ ሲጠይቁ ‹‹ትግሬ›› ሲሉ መለሱ። የምስክሩ መስቀለኛ ጥያቄ አላማ ቢያንስ የትግራይ ተወላጅን በትግራይ ላይ ማነሳሳት የሚለው ክስ አሳማኝ ሊሆን እንደማይችል ለችሎቱ ማሳየት ነው። የተሳካላቸውም ይመስለኛል። ነፃነት ደግሞ ጠየቀ ‹‹አቶ አዳነ የቀበሌ ሊቀመንበር አይደሉ እንዴ?››፤ ምስክሩ መለሱ ‹‹ነበርኩኝ አሁን ለቅቄያለሁ››፤ ነፃነት ቀጠለ ‹‹በምርጫው ወቅት የንብ ካኔቴራ ለብሰው ለኢህአዴግ ሲቀሰቅሱ አልነበረም?›› ምስክሩም መለሱ (ወይም ቀለዱ ብንለው ይሻላል) ‹‹የንብ ካኔቴራ ለብሼ ስቀሰቅስ የነበረው ለቅንጅት ነው አንተ ባዘዝከኝ መሰረት››
ሌላኛው ነጋዴ ነኝ ያለ ምስክር ደግሞ የመኢአድ አመራሮች መንዝ ላይ የታጠቀ ሀይል እንዲያደራጅ እንዳዘዙት መስክሮ ሲጨርስ ማሙሸት አማረ ሰውየው የመኢአድ አባል ሳይሆን የደብረብርሃን ወህኒ ቤት አዛዥ መሆኑን ገለፀ። አያይዞም ‹‹ፖሊስ የማንም አባል ፓርቲ መሆን እንደማይችል እየታወቀ እንዴት የመኢአድ አባል ሆንክ?›› ሲልም ጠየቀው። ምስክሩም ጥያቄውን በጥያቄ መለሰ ‹‹ፖሊስ የፓርቲ አባል መሆን እንደማይችል እያወክ ለምን መለመልከኝ?››
እንግዲህ በእንዲህ አይነት የሰነድ እና የሰው ማስረጃ ነው አቶ ሽመልስ ከማል ተከራክረው ተከሳሾቹ ጥፋተኛ የተባሉት። የሚገርመው ደግሞ ፍርድ ቤቱም የአባላዘር በሽታን የህክምና ማስረጃን ተቀብሎ ተከሳሾቹ ‹‹ህገ መንግስቱን በሀይል ለመናድ እና የዘር ማጥፋት ሙከራ አድርገዋል›› ሲል በማመኑ ነበር የእድሜ ልክ እስራት የፈረደው። …እነዚህ ዳኞች ዛሬስ የት ይሆኑ? በስራ ላይ ናቸው? አቃቤ ሕጉ እንኳ ምክትል ሚኒስትር ሆነዋል። ሹመት ያዳብርም ብለናል። እዚህች ጋ ቀኝ ጌታ ዮፍታዬ ንጉሴ የገጠሙትን ስንኝ አስታውሰን ወደሌላው እንለፍ፡-
ኢትዮጵያ ሀገሬ ሞኝ ነሽ ተላላ
የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ።
ከሽሮ ሜዳ አካባቢ ህገ መንግስቱን ንደዋል ተብለው የተያዙ ወጣቶች ላይ የቀረቡት ምስክር በልብስ ስፌት ስራ የሚተዳደሩ እና በወጣቶቹ ተደበደብኩ የሚሉ ናቸው። በእርግጥ አንድ ልብስ ሰፊን መደብደብ እንዴት ሆኖ መንግስት መገልበጥ እንደሆነ ባይታወቅም፣ ተደበደብኩ ያሉት ግለሰብ የሰጡት መልስ በራሱ ስለኢትዮጵያ ፍትህ ብቻውን የሚመሰክር ነው። ሰውየው መደብደባቸውን ከተናገሩ በኋላ ደበደቡ ከተባሉት ውስጥ እዛው ችሎት ላይ ሁለቱ መቼ እና የት እንደደበደቧቸው ሲጠይቋቸው ቃል በቃል እንዲህ አሉ፡-
‹‹…አንተም አልመታኸኝ፤ ሁላችሁም አልደበደባችሁኝም፤ ዓቃቤ ሕግ ነው እነርሱ ናቸው የደበደቡህ ያለኝ››
ይህን ጊዜ ደግሞ አቃቤ ህጉ ተከራከረ። ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በቶን የሚቆጠር ማስረጃ እንዳላቸው በይፋ ተናግረው፤ ዐቃቤ ህጉም በዚህ ማስረጃ የወንጀለኞቹን ጥፋት በችሎት እንዲያረጋግጥላቸው ልከውት ሲያበቁ፣ ዐቃቤ ህጋቸው ግን ከደቂቃ በፊት ምስክሬ ሲሉ በኩራት የአመጡአቸውን ግለሰብ እንዲህ አሉ፡-
‹‹…ፍ/ቤቱ የሰውዬውን የጤንነት ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባት ይመልከትልን››
መቼም ዓቃቤ ህጉ ያቀረብኩትን ምስክር ቅንጅቶች አሳበዷቸው እያለ እንዳልሆነ ተስፋ አደርጋለሁ። በዚህ መሀል ግን ዛሬም ‹‹ህገ-መንግስቱን ለመናድ ሞክረዋል›› እየተባሉ ቃሊቲ የሚወረወሩ ኢትዮጵያውያን የፍትህ ሁናቴ ያሳስበኛል፤ ምክንያቴ ደግሞ ቢያንስ ችሎቱን በእንዲህ አይነት ማስረጃ ለማሳሳት የሞከሩት ዐቃቢ ህጎች ላይ የተወሰደ ምንም አይነት ህጋዊ እርምጃ አለመኖሩ ነው። ነገንም በእጅጉ እንድንፈራ የሚያደርገን ይህ ነው። ድራማው ላለመደገሙ ምንም አይነት ዋስትና የለምና። ወህኒ ቤቱም ቢሆን ከዛ በኋላ አያያዙ ይበልጥ እየጠበቀ እንደሆነ የሚያሳዩ ምልክቶች አሉ፤ ለምሳሌ ከፖለቲካ ጋር በተያያዘ ለሚታሰሩ እስረኞች ሬዲዮን እና መንግስትን የሚተቹ መጸሀፍቶች እንዳይገቡ ተከልክሏል፤ የጠያቂ ቁጥርም ከሶስት እንዳያልፍ ተደርጓል።
የቃሊቲው ጭፍጨፋ
ይህ መጽሐፍ በብቁ ጋዜጠኛ የተፃፈ ለመሆኑ ውስጡን አይቶ ማረጋገጥ ይቻላል። ጥቃቅን ክስተቶች ሳይቀሩ ተለቅመው የተካተቱበት ነውና። ከዚህ ባለፈ በዚሁ ጉዳይ ላይ ከተፃፉ ሁሉ ለተመራማሪዎች በመረጃ አያያዙ የተሻለ ሊባል የሚችል እንደሆነ በድፍረት መናገር ይቻላል። እንዲሁም ፀሐፊው ራሱ እንዳለው በተለይ በቃሊቲ እስር ቤት የተገደሉት እስረኞች ዝርዝር አጣሪ ኮሚቴው ይፋ ካደረገው በብዙ እጥፍ እንደሚበልጥ እና ማጣራት የሚችል ሰው ካለ የገዳዮቹንም ስም በግል ሊሰጥ እንደሚችል እስከዛው ግን ገዳዮቹ ራሳቸውን ይሰውራሉ በሚል በሚስጥር እንደያዘው ገልጿል።
ስለግድያውም፡-
‹‹…ቀደም ብሎ እንደተጠቀሰው በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ጥቅምት 24/98 ዓ.ም. የተፈፀመውን ድርጊት ለማጣራት ኮሚሽኑ ተደጋጋሚ ሙከራ ያደረገ ቢሆንም፣ ጉዳዩ አሳሳቢና ልዩ ትኩረት የሚያስፈልገው ሆኖ ተገኝቷል፤ ስለዚህ መንግስት በባለሙያ እንዲታይ ያደርግ ዘንድ ኮሚሽኑ ያሳስባል›› ይላል ጥቅምት 20/1999 ዓ.ም በፓርላማው በዶ/ር መኮንን ዲሳሳ የሚመራው የአጣሪ ኮሚሽኑ ሪፖርት (በነገራችን ላይ የአጣሪው ኮሚሽን ስብሰቢ በቀጥታ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ የፀጥታ ሰራተኞች አሳደሩብኝ ባሉት ጫና ሀገር ጥለው ከተሰደዱ በኋላ ነው እኒህ ዶ/ር የተተኩት። በሪፖርቱ ላይም ድምፅ ከሰጡት ሰዎች ውስጥ ሁሉም አባላት ‹‹ፖሊስ ትርፍ ሀይል ተጠቅሟል›› ሲሉ፣ ዶ/ሩ እና ሼህ ኤልያስ ሬድዋን ብቻ ናቸው ‹‹ፖሊስ የተጠቀመው ሀይል ተመጣጣኝ ነው›› በማለት ድምፅ የሰጡት። መቼም የዶ/ሩስ ይሁን፣ ለፈጣሪዬ ያደርኩ ነኝ የሚሉት ሼህ ድምፅ ግን ያሳዝናል። ዳሩ የፀረ-መጅሊስ እንቅስቃሴንም እንዲህ ያሉ መሪዎች መሰሉኝ እያጨናገፉ ያሉት?)
ወደ ቃሊቲው ጭፍጨፋ ስንመለስ በአንድ ጊቢ ውስጥ ወደየትም እንዳይሸሹ በታጠቁ ፖሊሶች በሚጠበቁ እስረኞች ላይ የደረሰው ጭፍጨፋ በ17 ሰዎች ሞት ብቻ እንዳላባራ የሲሳይ አጌና መፅሐፍ ይከራከራል። መጽሐፉ ከገፅ 377-379 ድረስ በወቅቱ ተገደሉ ያላቸውን የ163 ሰዎች ስም እና እድሜ ዘርዝሮ በሰንጠረዥ አስቀምጧል። ‹‹122 የሚሆኑ የተገደሉት በዞን 3 ሲሆን፣ 56 ደግሞ በዞን 2 ነው።›› ይልና ‹‹ከእነዚህ ውስጥ ኃ/ማርያም አምባዬ፣ ደረጀ ማሞ፣ ታምሩ ኃ/መስቀል፣ ወጋየሁ ዘሪሁን፣ እንዳለ /ከወረዳ 3/፣ አበበ /ከአርሲ/፣ ዳንኤል ታደሰ መኝታቸው ላይ እንዳሉ የተገደሉ ናቸው›› ይለናል።
መቼም ይህ መጽሐፍ የአንድ ጋዜጠኛ ትርክት እንጂ የመርማሪ ኮሚቴው ሪፖርት ባለመሆኑ እንዳለ መቀበል ይቸግረናል። መንግስትም ሆነ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት በመጽሐፉ ላይ ተገድለዋል ተብለው ስለተዘረዘሩት 163 ሰዎች እውነት ነው ወይም ውሸት ነው ሲል በአሳማኝ ሁኔታ ሊያስተባብል ወይም አምኖ ኋላፊነቱን ሊወስድ ይገባል። አሊያ ዝምታን ከመረጠ የሲሳይን መጽሐፍ እንዳለ ልንቀበል እንገደዳለን። በአገሪቱም መንግስት ራሱ የሾማቸው አጣሪ ኮሚቴዎች በሪፖርታቸው ላይ ስለቃሊቲው ግድያ ሲያትቱ ‹‹ጉዳዩ አሳሳቢና ልዩ ትኩረት የሚያስፈልገው ሆኖ ተገኝቷል፤ ስለዚህ መንግስት በባለሙያ እንዲታይ ያደርግ ዘንድ ኮሚሽኑ ያሳስባል›› ማለታቸውን አስታውሰን ከአምስት አመት በኋላም ቢሆን አንዳች ለማጣራት የተደረገ ሙከራ አለመኖሩን ስናስተውል ልባችን ወደ ሲሳይ መጽሐፍ ያጋድላል።
‹‹የቃሊቲው መንግስት›› በብዙ መልኩ እስከዛሬ በጉዳዩ ላይ ከተፃፉ መፃሀፎች የተለየ ነው። ለምሳሌ በቃሊቲ ስለተደረገው ግድያ መነሻም ሲሳይ እንደ አንድ ጋዜጠኛ አጣርቶ የደረሰበትንም ያቀርብልናል።
‹‹ሀ-የግጭቱ መንስኤ›› በሚል ርዕስ ስር በቀረበው ፅሁፍ ላይ በቃሊቲ ጥቅምት 24/1998 ዓ.ም. ስለተከሰተው ግድያ መነሻ ዘርዝሯል። ‹‹ጥቅምት 23/1998 በአዲስ አበባ ከተማ የተፈጠረውን ረብሻ በተመለከተ በምሽት በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በፖሊሶች ላይ የደረሰውን ጉዳት የተመለከተ ዘገባ ሲቀርብ፣ በየዞኑ በተለይም በዞን 3 በሁሉም ቤት በድንገት ከፍተኛ ፉጨት ተሰማ፣ ጭብጨባም ተከተለ›› ይልና ፖሊሶቹ በዚህ ድርጊት ቅያሜ እንደያዙ አደሩ ይለናል። በማግስቱም ‹‹ዞን 2 የሚገኙ እስረኞች ለምን እንደሆነ ግልፅ ባልሆነ ሁኔታ አሸዋ የማረሚያ ቤቱ የዞኑ ተጠሪ ቤተሰቦቻችሁ የመረጡት ቅንጅትን አይደለም? ቅንጅት ይግዛላችሁ የሚል ምላሽ ይሰጣል። በዚህ ምላሽ የተበሳጨው ታምሩ የተባለ እስረኛ ለዞን ቀጠናው ጠንከር ያለ የቃላት ምላሽ ሲሰጥ የዞን ቀጠናው ይመታዋል። ይህም ለተቃውሞ መጀመር ምክንያት መሆኑ ተሰምቷል። ከዚህ በኋላ ወንድሞቻችን ሲያልቁ እኛ እዚህ ምን እናደርጋለን በማለት በዞን 3 አንደኛ ቤት ውስጥ ራሳቸውን ለማቃጠል በላያቸው ላይ እሳት የለኮሱ መኖራቸውም ተሰምቷል። ከዞን ሁለት የተወሰኑት እስረኞች ወደ ዞን 3 ግቢ ተሻግረው የተቃውሞ ድምፅ ሲያሰሙም የጥይት ተኩስ ይቀጥላል። ያለማቋረጥ በቀጠለው ተኩስ ሰዎች መውደቅ ሲጀምሩ እስረኛው ይበልጥ ስለመነሳቱ የሚናገሩ አሉ። በዚህ ረጅም ደቂቃዎች በፈጀው ተኩስ እክፍላቸው ውስጥ ቁጭ ያሉ፣ እንዲሁም መኝታቸው ላይ የነበሩ ሰለባ ስለመሆናቸውም መገንዘብ ተችሏል።›› ይላል የሲሳይ አጌና የምርመራ ሪፖርት።
መንግስት ደግሞ ሊያመልጡ ሙከራ ሲያደርጉ ነው የተገደሉት የሚል መግለጫ በወቅቱ አውጥቶ ነበር። እንግዲህ በእንዲህ አይነት ግድያ የተሳተፈ፣ የጎዳና ላይ ጭፍጨፋን እንደሰላማዊ ተቃውሞ መከላከያ ያደረገ (አጣሪ ኮሚቴው ሰላማዊ ሰልፈኞቹ ምንም አይነት የጦር መሳሪያ አለመያዛቸውን እና የባንክ ዘረፋ ሙከራ አለማድረጋቸውን ገልጿል) መንግስትን በመደገፍ የታላቋ ሀገር አሜሪካ ጉዳይ አመላላሾች ዶናልድ ያማማቶ እና ቪኪ ሒድልስተን አንዴ ብርሃኑ ነጋን ለብቻህ ወጥተህ አዲስ አበባን ተረከብ ብለው የመነጣጠል ሙከራ ሲያደርጉ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ የቅንጅት ተከሳሾችን ‹‹ህገ-መንግስቱን ተቀበሉ›› እያሉ በመወትወት የኢህአዴግን ፕሮፓጋንዳ ሲደግሙ በመጽሐፉ ላይ በትዝብት እናነባለን። ግራ የሚያጋባን ግን እነዚህ የአሜሪካ ወኪሎች በህገ መንግስቱ መሰረት የተመሰረተን እና በምርጫ የተሳተፈ ፓርቲን ወደ ኋላ ጎትተው ህገ- መንግስቱን ተቀበል ማለታቸው ነው።
የሲሳይ አጌና መጽሐፍ ያነሳቸውን ጭብጦች እንዲህ በአንድ አርቲክል መዳሰስም ሆነ ያላቸውን ፖለቲካዊ አንድምታ መተንተን አይቻልም። በዚህ ጥልቅ እና ጉዳዮችን በዝርዝር ባቀረበው መፅሐፍ ላይ እንደተጠቀሰው ሀገሪቷን የሚመሩት ሰዎች በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ እንኳን የሚገዳደራቸውን ኃይል ለመጨፍለቅ ሲሉ ምን ያህል ተቋማቱን እና ህግጋትን መቀለጃ እንደሚያደርጓቸው አንዳንዴ እያስፈገገን፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ደማችንን እያሞቀው እንድንታዘብ ያስችለናል። ኢህአዴግ ከሥልጣን እንዲወርድ ለአምላካቸው የተሳሉ አማኞችን ዘብጥያ የሚያወርድ፣ ለጨጓራ በሽታ መንስኤነት ቅንጅትን የሚጠራ አቃቤ ሕግ እና ይህን እንቶ ፈንቶ የሚያዳምጥ ፍርድ ቤት ይህችን ሀገር ወዴት ሊወስዳት ነው? ይህን የመሰለው ፍርድ ቤት ህዝባዊ እምነት ቢነፈገው ምንስ ይገርማል? በህግ ቁጥጥር ስር የዋሉ መቶ ስልሳ ሶስት ሰዎች በእስር ቤት ጠባቂ ፖሊሶች በተኙበት ጭምር ሲጨፈጨፉ ዝምታን የመረጠ ስራ አስፈፃሚን ምን ብለን ልንጠራው እንችል ይሆን? እኒህን ነገሮች እንዳሰላስል ያደረገኝን የጋዜጠኛው ወዳጄን መጽሐፍ አንብቤ ስዘጋ ‹‹እሪ በይ አገሬ›› የሚለው የደቡብ አፍሪካው ደራሲ አለን ፔተን ጩኸት የኔንም ነፍስ ሰቅዞ ያዘው።

No comments:

Post a Comment