"Food is nothing without freedom! We Need Freedom

”Food is nothing without freedom! We Need Freedom!

Friday 8 June 2012

የመነን 4ኛ ባል!





የመነን 4ኛ ባል!

        ከብዙ አመታት በፊት ተፈሪ መኮንን የሚባል አንድ ወጣት ደጃዝማች በሃረር አካባቢ ይኖር ነበር። እና ኑሮውን በሰላም በመኖር ላይ ሳለ አንድ ቀን ያልጠበቀው ነገር ገጠመው። ተፈሪ እንደወትሮው ጸሎት ላይ ሳለ ስልክ እንደሚፈልገው ተነገረው። የደወለለት የአጤ ምኒልክ ዙፋን ወራሽ ልጅ እያሱ ነበር። ሰላምታ ከተለዋወጡ በሁዋላ ልጅ እያሱ በቀጥታ ተፈሪን እንዲህ አለው፣
        “ስማ ተፈሪ! የእህቴን ልጅ መነን አስፋውን ልድርልህ ወስኛለሁ። የአንተ አሳብ ምንድነው?”
        ተፈሪ በጣም ደነገጠ።  ምክንያቱም መነን ከሶስተኛ ባሏ ጋር ከተጋባች ገና አንድ አመት እንኳ አልሞላትም ነበር። ከዚያ በፊት ካገባቻቸው ሁለት ባሎች በድምሩ አራት ልጆች መውለዷንም ያውቃል። አራት ልጆች ከወለደች በሁዋላ ሶስተኛ ባል አግብታ በመኖር ላይ ያለችን ሴት፣ “ልዳርልህ” የሚል አሳብ ሲቀርብለት ተፈሪ መደንገጡ የሚጠበቅ ነበር። እና ድንጋጤውን ዋጥ አድርጎ ጥያቄ አቀረበ፣
        “ጌታዬ! ለኔ የምታስብልኝን ሁሉ በደስታ መቀበል ፍላጎቴ ነው። ዳሩ ግን መነን የራስ ልኡልሰገድ ሚስት ናት። እንዴት ሆኖ ነው ለኔ የምትዳረው?”
        ልጅ እያሱ በቁጣ ቃል ምላሽ ሰጠ፣
        “እሱን ለኔ ተወው። አንተ እዚህ ውስጥ መግባት የለብህም። የጠየቅሁህ ‘መነንን ታገባታለህ ወይስ አታገባትም?’ የሚለውን ነው…”
        በዚህ ጊዜ ተፈሪ መኮንን ምላሹን ሰጠ፣
        “እሺ አገባታለሁ”
        “እንግዲያው በ15 ቀናት ውስጥ ሽማግሌ ወደአዲሳባ ላክልን። አንተ አዲሳባ መምጣት አያስፈልግህም። ሽማግሌዎቹ ሚስትህን ይዘውልህ ይመጣሉ።”
        ሁለቱ የባላባት ልጆች በዚህ መልኩ ስለመነን በሚነጋገሩበት ወቅት መነን ከሶስተኛ ባሏ እና ከአራት ልጆቿ ጋር በሰላም በመኖር ላይ ነበረች። ለአራተኛ ጊዜ ለሌላ ባል እዳራለሁ ብላ በህልምዋ እንኳ አሳቡ አልነበራትም። ከሶስተኛ ባሏ ጋር በፍቅርና በደስታ መኖር ጀምራ ነበር።
        ተፈሪ መኮንን ከልጅ እያሱ ጋር የስልክ ንግግሩን ካበቃ በሁዋላ በቀጥታ ወደ ፀሎቱ ነበር የተመለሰው። ፀሎቱን እንዳበቃም ከአባቱ ወዳጆችና ነባር መኳንንቶች ጋር በጉዳዩ ላይ መከሩበት። ጋብቻውን ከመቀበል ውጭ ምርጫ አልነበራቸውም። መነንን እንደ ሙሽራ በማጀብ ወደ አራተኛ ባሏ የሚያመጧትም አራት ሲህ ወታደሮች ወደ አዲስአበባ ተላኩ። ከሞቀ ትዳሯ እና ከሶስተኛ ባሏ ነጥለውም ወደ ሃረር ወስደው ለተፈሪ መኮንን ዳሯት። ወይዘሮ መነን ወደ ተዘጋጀላቸው አራተኛ ባል እንድትሄድ ስትጠየቅ፣ “አምላክ በዚሁ በቃሽ ይበለኝ” ከማለት ሌላ አንዳችም ቃል እንዳልተነፈሰች ይነገራል። በርግጥም አምላክ ፀሎቷን ሰምቶላታል።
        አጤ ሃይለስላሴ ተገደው እቴጌ መነንን ካገቡ በሁዋላ እስከ ህይወታቸው ፍፃሜ በጋብቻ ኖረዋል። እቴጌ መነንም ከአራተኛ ባላቸው በርካታ ልጆችን ለማፍራት በቅተዋል።
(የትረካ ምንጭ፣ ዘውዴ ረታ – ተፈሪ መኮንን)

No comments:

Post a Comment